ደቀ መዝሙር https://deqemezmur.com ደቀ መዝሙር መሆን ደቀ መዛሙርት ማድረግ Sun, 26 Mar 2023 02:29:54 +0000 en-US hourly 1 https://wordpress.org/?v=6.4.3 https://deqemezmur.com/wp-content/uploads/2022/08/cropped-photo_2022-08-09_18-28-03-32x32.jpg ደቀ መዝሙር https://deqemezmur.com 32 32 የዔድን ገነት ዛፍ ለምን አስፈለገ? https://deqemezmur.com/2023/03/26/why-the-tree-in-the-garden-of-eden/ Sun, 26 Mar 2023 02:29:54 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2207 እግዚአብሄር አዳምና ሄዋን እንደሚበሉና እንደሚወድቁ ካወቀ ወይም እያወቀ በኤደን ገነት ውስጥ ዛፍ ተክሎ አትብሉ ለምን አላቸው? የዛፏ መኖር ለምን አስፈለገ? (መ. መ) . . . . . መ. መ.፥ ይህ መሠረታዊ ጥያቄ ነው። እኔም ራሴ ገና አዲስ ክርስቲያን በነበርኩባቸው በርካታ ዓመታት (አሁንም፥ ሁሌም አዲስ ክርስቲያን ነኝ) ደጋግሜ ጠይቄአለሁ። የዚህን ጥያቄ መልስ አንኳር የወሰድኩት መጀመሪያ መጻፍ […]

The post የዔድን ገነት ዛፍ ለምን አስፈለገ? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
እግዚአብሄር አዳምና ሄዋን እንደሚበሉና እንደሚወድቁ ካወቀ ወይም እያወቀ በኤደን ገነት ውስጥ ዛፍ ተክሎ አትብሉ ለምን አላቸው? የዛፏ መኖር ለምን አስፈለገ? (መ. መ)

. . . . .

መ. መ.፥ ይህ መሠረታዊ ጥያቄ ነው። እኔም ራሴ ገና አዲስ ክርስቲያን በነበርኩባቸው በርካታ ዓመታት (አሁንም፥ ሁሌም አዲስ ክርስቲያን ነኝ) ደጋግሜ ጠይቄአለሁ። የዚህን ጥያቄ መልስ አንኳር የወሰድኩት መጀመሪያ መጻፍ ሀ ስል ከጻፍኩት (በኛ 1985) አዲስ ሕይወት የሚባል የትመማ መጽሐፍ ነው።

በመጀመሪያ የጥያቄው መነሻ የሆነውን ጥቅሱን በመጻፍ ልጀምር፤

እግዚአብሔር አምላክም ለማየት ደስ የሚያሰኘውን፥ ለመብላትም መልካም የሆነውን ዛፍ ሁሉ ከምድር አበቀለ፤ በገነትም መካከል የሕይወትን ዛፍ፥ መልካምንና ክፉን የሚያስታውቀውንም ዛፍ አበቀለ። ዘፍ. 2፥9። እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው፦ ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና። ዘፍ. 2፥16-17።

የዛፏ መኖር ለምን አስፈለገ ለሚለው ጥያቄ አጭሩ መልስ ትርጉም ላለው የፍቅር ግንኙነት ነው።

በተን አድርጎ ለመረዳት ደግሞ የግንኙነትን መስፈርት መረዳትን ይጠይቃል። ግንኙነት ሲባል የመጽሐፍ ቅዱሱ እግዚአብሔር ኅብረት አስፈልጎት ነበር ማለት አይደለም። እርሱ በዘላለማዊ ግንኙነትና ኅብረት ውስጥ የሚኖር አብ፥ ወልድ፥ መንፈስ ቅዱስ ሠለስቱ አካል፥ አሐዱ አምላክ ነው። እግዚአብሔር አዳምንና ሔዋንን፥ ወይም እኔንና አንተን የፈጠረው እርሱ ኅብረት አስፈልጎት ሳይሆን እኛ ኅብረት ይኖረን ዘንድ ነው። ዮሐንስ ስለዚህ ኅብረት ሲጽፍ በ1ዮሐ. 1፥3 እንዲህ ይላል፤ እናንተ ደግሞ ከእኛ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ ያየነውንና የሰማነውን ለእናንተ ደግሞ እናወራላችኋለን። ኅብረታችንም ከአባት ጋር ከልጁም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ነው።

ኅብረት ከእርሱ ጋር ይኖረው ዘንድ ሰውን መፍጠሩ ድንቅ የቸርነት ሥራው ነው። ሰውን መፍጠሩ ምንም ግዴታ ኖሮበት ሳይሆን እንዲያው የቸርነቱና የነጎነቱ ብዛት ብቻ ነው። መፍጠሩ ደግሞ እንዲያው እንደ እንስሳ ሁሉ በልቶና ጠጥቶ፥ ወልዶና አሳድጎ፥ ኖሮና ሞቶ ያለ መታሰቢያ እንዲቀር ሳይሆን ትልቁን ግንኙነት ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትን ያደርግ ዘንድ ነው። ለዚህም ነው ከእንስሳት የለየውን የራሱን እስትንፋስ እፍ ያለበት። የእግዚአብሔር እስትንፋስ ሰውን ከሌሎች ምድራውያን ፍጡራን ሁሉ ለይቶ ዘላለዋሚ ያደርገዋል፤ እግዚአብሔር ራሱ ዘላለማዊ ነውና።

ለግንኙነት ወይም ለኅብረት ደግሞ ፍቅርና ፈቃድ የግድ ያስፈልጋል። ለእንስሳዊ ግንኙነት ይህ አያስፈልግም። ለዚህ ደመ ነፍስ ብቻውን በቂ ነው። ለሰውና ሰው፥ እንዲሁም ለሰውና እግዚአብሔር ግንኙነት ግን ፍቅርና ፈቃድ ያስፈልጋሉ። ፍቅር ከፈቃድ የሚመነጭ ሲሆን ፈቃድ ራሱ ግን እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከሕይወት ቀጥሎ የሰጠው ትልቅ ስጦታ ይመስለኛል።

የዛፉ (መልካምና ክፉን የሚያስታውቀው ዛፍ) መኖር አስፈላጊነት እንግዲህ እዚህ ላይ ነው። ይህ ግንኙነት በፈቃድ ላይ የተመሰረተ ለመሆኑ ምስክር፥ መፈተሻ፥ ማረጋገጫ ያስፈልጋል። እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ፈቅዶና ወድዶ ነው። በእርሱ በኩል ፈቃድ አለ፤ መውደድም አለ። አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወድዶአልና ነው ቃሉ የሚለን። በዚህ ኅብረት ውስጥ በአዳም በኩልም የፈቃድና የፍቅር ግንኙነት ሊኖር ግድ ነው። ወድዶ ፈቅዶ የሚገባበት ግንኙነት ነው፤ ካልፈለገ፥ ካልወደደና ካልፈቀደ ላይገባ መብት አለው። ፈቃድ አለውና።  አዳምና ሔዋን በገነት ሲኖሩ ሙሉ ነጻነት ነበራቸው። የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ለመፈለግና ለመፈጸም፥ ኃጢአትንም ሳይሠሩ ለመኖር ችሎታ ነበራቸው።

እግዚአብሔር ሲጀመር አዳምንም፥ ዓለምንም ላይፈጥር ይችል ነበር። ዓለምም ባትፈጠር፥ እኛም ባንፈጠር ብለን እናስብ። ይህ ጥያቄም አይኖርም ነበር። ሌላው አማራጭ ዓለምን ፈጥሮ መልካምና ክፉ የሌለበት ማድረግ ወይም ስትፈጠርም መልካምና ክፉ የሚባል ነገር የሌለባት አድርጎ መፍጠር ነው። ይህ ደግሞ፥ ሁሉ ልክ የሚሆንበትና ትርጉም የሌለው እንስሳዊ ኑሮ እንደሚሆን መገመት አይሳነንም። ሌላው ምርጫ አዳምን መልካሙን ብቻ እንዲመርጥ አድርጎ መሥራት ነው። የዚህ ችግር ደግሞ ፈቃድ አልባነት ነው። አድርግ የተባለውን ያለ ምንም ምርጫ፥ ያለ ምንም ጥያቄ፥ አማራጭ ሳይኖር፥ ጥቅምና ጉዳት ሳይታወቅ፥ የግንኙነት ትርጉሙ ራሱም ሳይታወቅ፥ ልክ እንደ ሰው-ሠራሽ ሮቦት የተሠራበትን ተግባር ብቻ እንዲፈጽም፥ እንዲያደርግ ሆኖ ተሠራ ማለት ነው። ከሮቦት ጋር ግንኙነት መመሥረት አይቻልም። ሮቦት ነፍስና መንፈስ የለውም። ነፍስና መንፈስን መፍጠር የእግዚአብሔር ብቸኛ ሥልጣንና ችሎታ ነውና ሰው ነፍስን የመስራት ጥበብ ሊኖረውም አይችልም። የመጨረሻው አማራጭ በቃሉ ውስጥ የተጻፈውን አዳም መፍጠር ነው። ምርጫ ያለው፥ ፈቃድ ያለው፥ መታዘዝና አለመታዘዝ የሚችለውን፥ መውደድና አለመውደድ የሚችለውን አዳም መፍጠር። እግዚአብሔር ይህንን ነው ያደረገው። ማናችንም ከዚህኛው አማራጭ በፊት ያሉትን አማርጮች የምንፈልጋቸው አይመስለኝም።

ከአማራጮቹ ሁሉ እውነተኛ ኅብረትና ፍቅር ያለበት ግንኙነት ሊኖር የሚችለው በዚህ ፈቃድ ባለበት፥ ምርጫ ባለበት ግንኙነት ውስጥ ብቻ ነው። ምርጫ የመኖሩ አስፈላጊነት እግዚአብሔር የሚፈልገው በምርጫችን የምንግገዛለት ሲሆን ነው።

አዳምን ሲፈጥር ምንም ምርጫ ስለሌለው ሳይሆን ሙሉ የምርጫ ፈቃድ እያለው፥ ግን በፈቃደኝነት እንዲወድደው እግዚአብሔር ስለፈለገ በዔድን ገነት ውስጥ እንዳይበላ ያዘዘውን ዛፍ አኖረ። ይህም እግዚአብሔርን ታዝዞ በኅብረት እንዲኖር ወይም እግዚአብሔርን መታዘዙ በአዳም ፈቃድ ላይ እንዲመሠረት ስለወደደ ነው። አሳዛኙ ክስተት፥ አዳምና ሔዋን ለጥቂት ጊዜ (ምን ያህል መሆኑ አይታወቅም) እግዚአብሔርን ወደው ከተከተሉ በኋላ አለመታዘዝን መረጡ። እናም ውድቀት ሆነ። እዚህ ላይ፥ ‘ሰይጣን ባያስታቸው ኖሮ አይወድቁም ነበር፤ በመጀመሪያ ሰይጣን ለምን ተፈጠረ?’ ሊባል ይችላል። የዚህም መልስ ከላይ እንደተመለሰው ያለ ተመሳሳይ ነው። ሰይጣን ሲፈጠር ሰይጣን ሆኖ አልተፈጠረም፤ እርሱም እንደ ሰው ሁሉ ፈቃድ ያለው መልአክ ነበረ። እርሱም ፈቃዱን ተለማምዶ፥ አለመታዘዝን መርጦ የወደቀ ፍጡር ነው። ለአዳምና ሔዋን አለመታዘዝ ሳቢያው፥ ፈተናውን አቅራቢው ሰይጣን ሆነ እንጂ ውሳኔው የነ አዳም ነው። እምቢ ማለት ይችሉ ነበርና። ምርጫና ፈቃድ ነበራቸውና። ሰይጣን ባይፈትናቸውም ፈቃዳቸው አንድ ቀን ይጠይቃቸው ነበርና። የዛፉ (መልካምና ክፉን የሚያስታውቀው ዛፍ) መኖር አስፈላጊነት እንግዲህ ለዚህ ነው።

ዘላለም።

The post የዔድን ገነት ዛፍ ለምን አስፈለገ? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
በአዲስ ኪዳን አሥራት መስጠት ግዴታ ነው? https://deqemezmur.com/2023/03/26/is-tithing-for-new-testament-believers/ Sun, 26 Mar 2023 02:15:10 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2201 ከጥያቄዎች፤ በአዲስ ኪዳን አሥራት መስጠት ግዴታ ነው? የጌታ ፀጋ ይብዛልህ! በአዲስ ኪዳን አስራት መክፈል ግዴታ ነው ወይ! Some teacher saying that it is the law given to old covenant era! what is your understanding regarding to this idea? Thank you for kind response? your brother in Christ Jesus muluneh! ሙሉነህ፥ አሥራት መክፈል . . . […]

The post በአዲስ ኪዳን አሥራት መስጠት ግዴታ ነው? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ከጥያቄዎች፤ በአዲስ ኪዳን አሥራት መስጠት ግዴታ ነው?

የጌታ ፀጋ ይብዛልህ! በአዲስ ኪዳን አስራት መክፈል ግዴታ ነው ወይ! Some teacher saying that it is the law given to old covenant era! what is your understanding regarding to this idea? Thank you for kind response? your brother in Christ Jesus muluneh!

ሙሉነህ፥ አሥራት መክፈል . . . ብለው የሚጠይቁ ሰዎችን ስሰማ ግፊታቸውን ማወቅ እፈልጋለሁ። ብዙ ጊዜ ይህን ጥያቄ የሚያቀርቡ ሰዎች ለመስጠት የሚጓጉ ሳይሆኑ ከመስጠት የሚሸሹ ናቸው። እነዚህ ሰዎች ሲጠይቁ ለመስጠት ነው ወይስ ላለመስጠት? እቅጩን አሥራት ላይ ለማቆም ነው ወይስ ከዚያ ያነሰ ወይም ያለፈ ለመስጠት? አንዳንዶች ግን እውነቱን ማወቅ የሚሹ ናቸው። ይህኛውን እንደዚህኛው እወስዳለሁ። ግፊታችንን ማወቁ ይጠቅመናል።

ሁለት ጉልህ ቃላት ላይ ላተኩር። የመጀመሪያው ክፍያ የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ግዴታ የሚለው ነው።  አስራት ክፍያ አይደለም። መክፈል ለተደረገ አገልግሎት የሚደረግ ተመጣጣኝ የገንዘብ ወይም የሌላ ነገር እኩያ ልዋጭ ነገር ነው። ገበያ ሄደህ የበግ ግልገል ወስደህ 500 ብር ብትከፍል ወይም በወሩ መጨረሻ ለተጠቀምክበት ውኃ ወይም ስልክ 2ሺህ ብር ብትከፍል ለተቀበልከው ነገር የሰጠኸው ልዋጭ ነው። አሥራት በአዲስ ኪዳን ይቅርና በብሉይ ኪዳንም የኪዳኑ ሰዎች የመሆን አንድ መግለጫ እንጂ የተቀበሉት በጎነት ክፍያ አይደለም። ለምሳሌ ለምንሞቀው ፀሐይ ወይም ለምንተነፍሰው አየር አሥራት በምንም መልኩ ተመጣጣኝ ዋጋ አይደለም።

ሁለተኛ ግዴታ ላልከው ከላይ እንዳልኩት በብሉይ ኪዳንም የኪዳን ትስስር ምልክት እንጂ ግዴታ አይደለም። ለዚህ ነው አሥራቱን ይከለክሉ፥ ይሰርቁ የነበረው። በአዲሱ ኪዳን ደግሞ ምንም ነገር በግዴታ አይደረግም። ግዴታ ከሆነ ፈቃድ የለበትም። እግዚአብሔር ደግሞ በፈቃዳችን ላይ የሚጫን ጨቋኝ አምላክ አይደለም።

ይህን ካልኩ በኋላ አሥራት ምን መሆኑን እንይ። አሥራት በብሉይ እና አዲስ ኪዳን መጻሕፍት የተጻፈ ቃል ነው። አሥራት (מַעֲשֵׂר ማዓሤር ወይም מַעַשׂרָה ማዓሥራህ፤ עָשַׂר ዓሣር፤ δεκάτη ዴካቴ፤ ἀποδεκατόω አፖዴካተኦ) ከአሥር አንድ፤ ከአሥር አንድ እጅ፥ አንድ አሥረኛ ማለት ነው፤ ዘፍ. 14፥20፤ ዕብ. 7፥1-9። አይሁድ የኪዳኑ ሰዎች እንደመሆናቸው ከእጃቸው ፍሬ ሁሉ አሥራትን ለእግዚአብሔር እንዲያቀርቡ በሕጉ ታዝዘዋል፤ ዘሌ. 27፥30፤ ዘዳ. 14፥22-28፤ 2ዜና. 31፥5-6፤ ነህ. 10፥37-38፤ 13፥5-12፤  አይሁድ የሚሰጡት አሥራት ለሌዋውያን እንደ ርስት ሆኖ የሚቀርብ ነው፤ ዘኁ. 18፥21-24። ሌዋውያን ራሳቸውም ከሚቀበሉት አሥራት፥ የአሥራት አሥራት የማንሣት ቁርባን አድርገው ያቀርባሉ፤ ዘኁ. 18፥26-28። ለሌዋውያን ከሚሰጠው በተጨማሪ በሦስት ዓመት አንዴ ከሌዋዊው ጋር ለመጻተኛ፥ ለድሀ አደግና ለመበለት ይሰጣሉ፤ ዘዳ. 26፥12። ነገሥታትም አሥራት ይወስዳሉ፤ 1ሳሙ. 8፥15-17። አሥራትን ለእግዚአብሔር ቤት አለመስጠት እግዚአብሔርን መስረቅ ነው፤ ሚል. 3፥8-10።

አሥራት የሕጉ ትእዛዝ ብቻ ሳይሆን ከሕግም ይቀድማል፤ ዘፍ. 14፥20፤ ዕብ. 7፥1-9። በቀረቤታ ስናየው በብሉይ ኪዳን አይሁድ አሥራት ወይም አንድ አሥረኛ ብቻ ሳይሆን ከዚያ በጣም ያለፈ ነበር የሚሰጡት። ሕጉ አስሰጪ ነው፤ መስጠትን ያበረታታል። ኪዳኑ ደግሞ ሰጪ ነው። ቢታዘዙ በረከት ተቋጥሮበታልና። ያ በሕግ ዘመን ነው።

በአዲስ ኪዳን ሰዎች አሥራትንም ይሰጡ ነበር፤ ማቴ. 23፥23፤ ሉቃ. 11፥42፤ 18፥12። ሰዎች አሥራትን መስጠታቸውን ጌታ አላወገዘም። ይልቅስ ያወገዘው ከጥቃቅኑም አሥራት መስጠትን እየሰጡ ትልልቁን ነገር፥ ፍርድን፥ ምሕረትን፥ ታማኝነትን፥ እግዚአብሔርን መውደድን ስለሚተዉና በዚህ ስለሚተላለፉ ያንን ነው የወቀሰው። ሕጉ የተሰጣቸው አሥራት ከሰጡ ልጁ የተሰጠን ደግሞ ምንኛ ከዚያ በላይ መስጠት አይኖርብንም? ይሁን እንጂ፥ የአዲስ ኪዳን ስጦታ መሥዋዕት ሆኖ በደስታ፥ በፈቃድ፥ እና በልግሥና የሚሰጡት ስጦታ ነው፤ ሮሜ. 12፥8፤ 2ቆሮ. 9፥6-7፤ ፊል. 4፥18፥19። ግዴታ ከኖረ ሕግ ነው፤ እኛ ደግሞ ከሕግ በታች አይደለንም። ግዴታ ከኖረ ቅሬታም ይኖራል። ግዴታ ከሆነ እንደተጠየቀው ክፍያም ይመስላል፤ ከሆነ ደግሞ እጅ በጅ ልንል ነው፤ ዱቤ አይፈቀድም ውስጥ ልንገባ ነው።

በአዲስ ኪዳን እንደ መሥዋዕት አድርገን እንድናቀርብ የተነገሩን ነገሮች አሉ፤ 1ጴጥ. 2፥5 እናንተ ደግሞ እንደ ሕያዋን ድንጋዮች ሆናችሁ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕትን ታቀርቡ ዘንድ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ። ይላል። እኛ የአዲስ ኪዳን አማኞች ሁላችንም ካህናት ነንና መሥዋዕት አቅራቢዎች ነን። የምናቀርባቸው መሥዋዕቶች እነዚህ ናቸው፤

  1. ሰውነታችን፤ እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እለምናችኋለሁ፥ እርሱም ለአእምሮ የሚመች አገልግሎታችሁ ነው። ሮሜ. 12፥1፤ 15፥15-16።
  2. ምስጋናችን፤ እንግዲህ ዘወትር ለእግዚአብሔር የምስጋናን መሥዋዕት፥ ማለት ለስሙ የሚመሰክሩ የከንፈሮችን ፍሬ፥ በእርሱ እናቅርብለት። ዕብ. 13፥15።
  3. መልካምማድረግና ለሌሎች ማካፈላችን፤ ነገር ግን መልካም ማድረግን ለሌሎችም ማካፈልን አትርሱ፤ እንዲህ ያለው መሥዋዕት እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘዋልና። ዕብ. 13፥16።
  4. ለወንጌል ሥራ የምንሰጠው ስጦታችን፥ ገንዘባችን፤ ነገር ግን ሁሉ አለኝ ይበዛልኝማል፤ የመዓዛ ሽታና የተወደደ መሥዋዕት የሚሆነውን ለእግዚአብሔርም ደስ የሚያሰኘውን ስጦታችሁን ከአፍሮዲጡ ተቀብዬ ተሞልቼአለሁ። ፊል. 4፥18።
  5. ነፍሳችንም፤ ከላይ የተዘረዘሩት ሁላችንንም የሚመለከቱ ሲሆኑ ይህ ለሁሉም አይደለም፤ ሲጠየቅ ግን ለመሠዋት ማፈግፈግ የሌለብን መሥዋዕት ነው። በመሥዋዕት እንደሚደረግ፥ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና፥ የምሄድበትም ጊዜ ደርሶአል። 2ጢሞ. 4፥6። ነገር ግን በእምነታችሁ መሥዋዕትና አገልግሎት ተጨምሬ ሕይወቴ እንኳ ቢፈስ፥ ደስ ብሎኛል፤ ከሁላችሁም ጋር አብሬ ደስ ብሎኛል፤ ፊል. 2፥17።

ከላይ ካየናቸው መሥዋዕቶች አንጻር ሲታይ አሥራት ለጌታና ለቤቱ ሥራ የምንሰጠው ትንሹ ስጦታችን ነው። የመቄዶንያ ሰዎች ከብልጽግናቸው ሳይሆን ከድህነታቸው የሰጡት የመስጠትን በረከት ስለተለማመዱ ነው፤ 2ቆሮ. 8 እና 9። መስጠት ደግሞ በረከት ብቻ ሳይሆን ብጽዕናም ነው፤ እንዲሁ እየደከማችሁ ድውዮችን ልትረዱና እርሱ ራሱ፦ ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው እንዳለ የጌታን የኢየሱስን ቃል ልታስቡ ይገባችሁ ዘንድ በሁሉ አሳየኋችሁ። ሐዋ. 20፥35። በአዲስ ኪዳን አሥራት በግዴታ አይከፈልም፤ በፍቅር ግን ይሰጣል።

ዘላለም።

The post በአዲስ ኪዳን አሥራት መስጠት ግዴታ ነው? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
እግዚአብሔር ይጸጸታልን? https://deqemezmur.com/2023/03/15/does-god-regret/ Wed, 15 Mar 2023 23:48:19 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2193 መጽሐፍ ቅዱስ ከ10 ጊዜያት በላይ እንደተጸጸተ ይናገራል። እነዚህን ጥቅሶች ስናነብብ ይህን እናገኛለን። ዘፍ. 6፥6-7 እግዚአብሔርም ሰውን በምድር ላይ በመፍጠሩ ተጸጸተ፥ በልቡም አዘነ። እግዚአብሔርም፦ የፈጠርሁትን ሰው ከምድር ላይ አጠፋለሁ፥ ከሰው እስከ እንስሳ እስከ ተንቀሳቃሽም እስከ ሰማይ ወፍም ድረስ ስለ ፈጠርኋቸው ተጸጽቼአለሁና አለ። 1ሳሙ. 15፥10-11 እና 35 የእግዚአብሔርም ቃል፦ ሳኦል እኔን ከመከተል ተመልሶአልና፥ ትእዛዜንም አልፈጸመምና ስላነገሥሁት ተጸጸትሁ […]

The post እግዚአብሔር ይጸጸታልን? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
መጽሐፍ ቅዱስ ከ10 ጊዜያት በላይ እንደተጸጸተ ይናገራል። እነዚህን ጥቅሶች ስናነብብ ይህን እናገኛለን።

ዘፍ. 6፥6-7 እግዚአብሔርም ሰውን በምድር ላይ በመፍጠሩ ተጸጸተ፥ በልቡም አዘነ። እግዚአብሔርም፦ የፈጠርሁትን ሰው ከምድር ላይ አጠፋለሁ፥ ከሰው እስከ እንስሳ እስከ ተንቀሳቃሽም እስከ ሰማይ ወፍም ድረስ ስለ ፈጠርኋቸው ተጸጽቼአለሁና አለ።

1ሳሙ. 15፥10-11 እና 35 የእግዚአብሔርም ቃል፦ ሳኦል እኔን ከመከተል ተመልሶአልና፥ ትእዛዜንም አልፈጸመምና ስላነገሥሁት ተጸጸትሁ ብሎ ወደ ሳሙኤል መጣ። ሳሙኤልም ተቈጣ፤ ሌሊቱንም ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ጮኸ። . . . ሳኦልም ወደ ቤቱ ወደ ጊብዓ ወጣ፦ ሳሙኤልም እስከ ሞተበት ቀን ድረስ ሳኦልን ለማየት ዳግመኛ አልሄደም፥ ሳሙኤልም ለሳኦል አለቀሰ፤ እግዚአብሔርም በእስራኤል ላይ ሳኦልን ስላነገሠ ተጸጸተ።

1ዜና 21፥15፤ እግዚአብሔርም ያጠፋት ዘንድ ወደ ኢየሩሳሌም መልአክን ሰደደ፤ ሊያጠፋትም በቀረበ ጊዜ እግዚአብሔር አይቶ ስለ ክፉው ነገር ተጸጸተ፥ የሚያጠፋውንም መልአክ፦ በቃህ አሁን እጅህን መልስ አለው። የእግዚአብሔርም መልአክ በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ አጠገብ ቆሞ ነበር።

መዝ. 106፥45፤ ለእነርሱም ኪዳኑን አሰበ፥ እንደ ምሕረቱም ብዛት ተጸጸተ።

ኤር. 18፥8፥10፤ ይህ ስለ እርሱ የተናገርሁበት ሕዝብ ከክፋቱ ቢመለስ፥ እኔ አደርግበት ዘንድ ካሰብሁት ክፉ ነገር እጸጸታለሁ። በፊቴ ክፉን ነገር ቢያደርግ ቃሌንም ባይሰማ፥ እኔ አደርግለት ዘንድ ስለ ተናገርሁት መልካም ነገር እጸጸታለሁ።

ኤር. 42፥10፤ ስላደረግሁባችሁ ክፉ ነገር ተጸጽቻለሁና በዚህች ምድር ብትቀመጡ እሠራችኋለሁ እንጂ አላፈርሳችሁም፥ እተክላችኋለሁ እንጂ አልነቅላችሁም።

ኢዩ. 2፥13-14፤ ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ አምላካችሁም እግዚአብሔር ቸርና መሐሪ፥ ቍጣው የዘገየ፥ ምሕረቱም የበዛ፥ ለክፋትም የተጸጸተ ነውና ወደ እርሱ ተመለሱ። የሚመለስና የሚጸጸት እንደ ሆነ፥ ለአምላካችሁም ለእግዚአብሔር የእህልና የመጠጥ ቍርባን የሚሆነውን በረከት የሚያተርፍ እንደ ሆነ ማን ያውቃል?

አሞ. 7፥3፥6፤ እግዚአብሔርም ስለዚህ ነገር ተጸጸተ፤ ይህ አይሆንም፥ ይላል እግዚአብሔር። . . . እግዚአብሔርም ስለዚህ ነገር ተጸጸተ፤ ይህ ደግሞ አይሆንም፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

ዮና. 3:9-10፤ 4፥2፤ እኛ እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ተመልሶ ይጸጸት እንደ ሆነ፥ ከጽኑ ቍጣውም ይመለስ እንደ ሆነ ማን ያውቃል? እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውን አየ፤ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም። . . . ወደ እግዚአብሔርም ጸለየና፦ አቤቱ፥ እለምንሃለሁ፤ በአገሬ ሳለሁ የተናገርሁት ይህ አልነበረምን? አንተ ቸርና ይቅር ባይ፥ ታጋሽም፥ ምሕረትህም የበዛ፥ ከክፉው ነገርም የተነሣ የምትጸጸት አምላክ እንደ ሆንህ አውቄ ነበርና ስለዚህ ወደ ተርሴስ ለመኰብለል ፈጥኜ ነበር።

መጸጸት ለሰው ሲሆን ስሕተትን፥ መመለስን፥ መታረምን ያሳያል። እግዚአብሔር ተጸጸተ ሲባል እግዚአብሔር ተሳስቶ ነበር፥ እርማት አስፈልጎት ነበር ማለት ነው? ይህ ከሆነ እግዚአብሔር ይስታል ወይም ይሳሳታል ማለት ነው። ነገር ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በርካታ ጥቅሶች እግዚአብሔር አይጸጸትም ይላሉ። ለምሳሌ፥ ዘኁ. 23፥19፤ 1ሳሙ. 15፥29፤ መዝ. 110፥4፤ 132፥11፤ ኤር. 4፥28፤ 20፥16፤ ሕዝ. 24፥14፤ ዘካ. 8፥14፤ ሮሜ 11፥29፤ ዕብ. 7፥20-21። እነዚህ ጥቅሶች በግልጽ እግዚአብሔር አይጸጸትም ይላሉ። ስለዚህ ቃሉ እርስ በርሱ ይጋጫል ማለት ነው? ወይስ እውነት እግዚአብሔር ይጸጸታል?

መጸጸት ማለት ለሰው ሲነገር መሳሳትን ማስተዋል፥ ትክክል እንዳልሆኑ ወይም እንዳላደረጉ ማወቅ፥ መቆጨት፥ ከስሕተት መመለስ  ማለት ነው። መጸጸት ለእግዚአብሔር ከተነገረና በተመሳሳይ ትርጉም ካገናዘብነው እግዚአብሔርነቱን ያዋርዳል። ምክንያቱም እግዚአብሔር ፍጹም ነው። ሁሉን አዋቂም ነው። ስለዚህም ሰው በሚሳሳትበት መንገድ ሊሳሳት ከቶም አይታሰብምና አይጸጸትም።

እግዚአብሔር ተጸጸተ ሲባል መታረሙን ወይም ራሱን ማረሙን ማሳየቱ ነው? አይደለም። እዚህ ጸጸት የተባለው ቃል נָחַם (ናኻም) የሚል ነው። ቃሉ እህህ! ማለት ማዘን፥ መራራት ማለት ነው። በብዙ ጥቅሶች መጽናናት እና ማጽናናት የተባለው ቃል ይህ ነው። ናሆም፥ ነህምያ፥ ኑሐሚን የሚባሉት ስሞች ምንጫቸው ይህ ቃል ነው። በበርካታ ጥቅሶች ውስጥም ቃሉ ማጽናናት ወይም መጽናናት እየተባለ ተጠቅሶአል፤ ለምሳሌ፥ ዘፍ. 37፥35፤ ሩት 2፥13፤ ኢሳ. 12፥1፤ 61፥2፤ ወዘተ። መጽናናት ወይም ማጽናናት እንደምናውቀው ከኀዘን ጋር የተቆራኘ ቃል ነው። ተጸጸተ የሚለው ቃል ከላይ እንዳየነው መሳሳት ሳይሆን ማዘን ወይም መራራት መሆኑን ለማየት ጥቂት በዚህ ትርጉም የተጠቀሱትን የዚህን ተመሳሳይ ቃል נָחַם (ናኻም) አጠቃቀሶች እንመልከት።

ዘጸ. 32፥12 እና 14፤ ግብፃውያንስ፦ በተራራ መካከል ሊገድላቸው፥ ከምድርም ፊት ሊያጠፋቸው ለክፋት አወጣቸው ብለው ስለ ምን ይናገራሉ? ከመዓትህ ተመለስ፥ ለሕዝብህም በክፋታቸው ላይ ራራ። እግዚአብሔርም በሕዝቡ ላይ ሊያደርግ ስላሰበው ክፋት ራራ።

ኢሳ. 49፥13፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን አጽናንቶአልና፥ ለችግረኞቹም ራርቶአልና ሰማያት ሆይ፥ ዘምሩ፥ ምድር ሆይ፥ ደስ ይበልሽ ተራሮችም ሆይ፥ እልል በሉ።

በነዚህ ጥቅሶች መራራት የሚለው ቃል እና ቀደም ሲል ያየነው ተጸጸተ የሚለው አንድ ናቸው።

ዘዳ. 32፥36፤ ኃይላቸውም እንደ ደከመ፥ የተዘጋ የተለቀቀም እንደሌለ ባየ ጊዜ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ይፈርዳል፥ ስለ ባሪያዎቹም ያዝናል።

መሳ. 2፥18፤ እግዚአብሔርም መሳፍንትን ባስነሣላቸው ጊዜ እግዚአብሔር ከመስፍኑ ጋር ነበረ፤ እግዚአብሔርም ስለሚጋፉአቸውና ስለሚያስጨንቋቸው በጩኸታቸው ያዝን ነበርና በመስፍኑ ዘመን ሁሉ ከጠላቶቻቸው እጅ አዳናቸው።

2ሳሙ. 24፥16፤ የእግዚአብሔርም መልአክ ኢየሩሳሌምን ያጠፋት ዘንድ እጁን በዘረጋ ጊዜ እግዚአብሔር ስለ ክፉው ነገር አዘነ፥ ሕዝቡንም የሚያጠፋውን መልአክ፦ እንግዲህ በቃህ እጅህን መልስ አለው። የእግዚአብሔርም መልአክ በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ አጠገብ ነበረ። ይኸው ታሪክ በተጻፈበት ሌላ ስፍራ፥ በ1ዜና 21፥15፤ እግዚአብሔርም ያጠፋት ዘንድ ወደ ኢየሩሳሌም መልአክን ሰደደ፤ ሊያጠፋትም በቀረበ ጊዜ እግዚአብሔር አይቶ ስለ ክፉው ነገር ተጸጸተ፥ የሚያጠፋውንም መልአክ፦ በቃህ አሁን እጅህን መልስ አለው። የእግዚአብሔርም መልአክ በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ አጠገብ ቆሞ ነበር። በ2ሳሙ. 24፥16 አዘነ የተባለው ተመሳሳይ ቃል ነውና በ1ዜና 21፥15 ተጸጸተ ተብሎአል።

በእነዚህ ጥቅሶች ያለው ማዘን የሚለው ቃል እና ተጸጸተ የሚለው አንድ ናቸው።

ኤር. 15፥6፤ አንቺ እኔን ጥለሻል፥ ይላል እግዚአብሔር፥ ወደ ኋላሽም ተመልሰሻል፤ ስለዚህ እጄን በአንቺ ላይ ዘርግቼ አጥፍቼሻለሁ፤ ከይቅርታ ደክሜአለሁ።

ይቅርታ የሚለው ቃል እና ተጸጸተ አንድ ናቸው።

ኤር. 26፥3፥13፤ 26፥19፤ ምናልባት ይሰሙ፥ ከክፉ መንገዳቸውም ይመለሱ ይሆናል፤ እኔም ስለ ሥራቸው ክፋት ያሰብሁባቸውን ክፉ ነገር እተዋለሁ። . . . አሁንም መንገዳችሁንና ሥራችሁን አሳምሩ፥ የአምላካችሁንም የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ እግዚአብሔርም የተናገረባችሁን ክፉ ነገር ይተዋል። . . . በውኑ የይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስና ሕዝቡ ሁሉ ገደሉትን? በውኑ እግዚአብሔርን አልፈሩምን? ወደ እግዚአብሔርስ አልተማለሉምን? እግዚአብሔርስ የተናገረባቸውን ክፉ ነገር አይተውምን? እኛም በነፍሳችን ላይ ታላቅ ክፋት እናደርጋለን።

እዚህ መተው የተባለው ከመጸጸት ጋር አንድ ቃል ነው።

ሲጠቃለል፥ መጸጸት ማለት ለሰው ሲነገር መሳሳትን ማስተዋል፥ ትክክል እንዳልሆኑ ወይም እንዳላደረጉ ማወቅ፥ ከስሕተት ለመምመለስ ብሎ መቆጨት ማለት ነው። መጸጸት ለእግዚአብሔር ከተነገረና በተመሳሳይ ትርጉም ካገናዘብነው እግዚአብሔርነቱን ያዋርዳል። ምክንያቱም እግዚአብሔር ፍጹም አይደለም ያሰኛል። እግዚአብሔር ግን ፍጹም አምላክ ነው። ሁሉን አዋቂም ነው። ስለዚህም ሰው በሚሳሳትበት መንገድ ሊሳሳት ከቶም አይታሰብምና አይጸጸትም። ነገር ግን ያዝናል፤ ይራራል፤ ይቅር ይላል፤ ይተዋል። ይህ ማዘን፥ መራራት፥ ይቅር ማለት፥ እና መተው ነው በአማርኛ መጸጸት የተባለው።

ዘ. መ.

The post እግዚአብሔር ይጸጸታልን? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ታላቅ ሩጫ https://deqemezmur.com/2023/03/15/grand-run/ Wed, 15 Mar 2023 23:26:45 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2189 ሁላችን ሯጮች ነን። ዛሬ እሁድ ጥር 15 2014 (Jan, 23, 2022) በአዲስ አበባ ታላቁ ሩጫ ይደረጋል። ይህን ስጽፍ ሊጀምር አንድ ሰዓት ይቀረዋል። ለምን ታላቁ እንደተባለ አላውቅም። ‘ታላቅ’ ሳይሆን፥ ‘ታላቁ’ ነው የሚባለው። በእርግጥ ከአፍሪቃ የጎዳና ሩጫዎች ትልቁ ነው። ያ ይሆን ታላቁ ያስባለው? አላውቅም። ከእርሱ የሚበልጡ አሉ። 21 ዓመት ሆነው። ‘ዓላማው እስፖርትን ሩጫን ማበረታታት፥ ተተኪ አትሌቶችን ማፍራት፥ […]

The post ታላቅ ሩጫ first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ሁላችን ሯጮች ነን።

ዛሬ እሁድ ጥር 15 2014 (Jan, 23, 2022) በአዲስ አበባ ታላቁ ሩጫ ይደረጋል። ይህን ስጽፍ ሊጀምር አንድ ሰዓት ይቀረዋል።

ለምን ታላቁ እንደተባለ አላውቅም። ‘ታላቅ’ ሳይሆን፥ ‘ታላቁ’ ነው የሚባለው። በእርግጥ ከአፍሪቃ የጎዳና ሩጫዎች ትልቁ ነው። ያ ይሆን ታላቁ ያስባለው? አላውቅም። ከእርሱ የሚበልጡ አሉ። 21 ዓመት ሆነው። ‘ዓላማው እስፖርትን ሩጫን ማበረታታት፥ ተተኪ አትሌቶችን ማፍራት፥ በጎ መልእክቶችን ማስተላለፍ፥ ኢትዮጵያን በበጎ ማስተዋወቅና ቱሪዝምን ማስፋፋት ነው።’ እንደ አስተባባሪዋ። የዘንድሮው በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ቀኑ ተራዝሞአል። ባይለወጥ ኅዳር 5 ነበር ሊደረግ የነበረው። በዛሬው ወደ 25 ሺህ ሯጮች ይጠበቃሉ።

የሚደረግበት ቀን እሁድ ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ጀምሮ ቢሆንም ከጠዋቱ 11:30 (5:30 a.m.) ጀምሮ ብዙ መንገዶችና ጎዳናዎች ይዘጋሉ። እሁድ ነውና አምልኮም ይስተጓጎላል።

ሩጫ መልካም ነው። ይህ ሩጫም መልካም ነው። ማናቸውም ሩጫም መልካም ነው። ሕይወት ራሷ ሩጫ ናት።

ሁላችን ሯጮች ነን፤
ሁሌ እንሮጣለን፤
ከእንጀራችን ኋላ፤
ምንም አሸንፈን ዋንጫውን ባንበላ።

ብሏል ባለቅኔ ደረጀ በላይነህ።

ሐዋርያው ጳውሎስ፥ መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፥ ሩጫውን ጨርሼአለሁ፥ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ (2ጢሞ. 4፥7) ሲል፥ ለሟቾች የመቃብር ድንጋይ ሐረግ መጣሉ አይደለም። እውነትም ሩጫውን የሮጠ ሰው ነው።

እኛም ሁላችን በሩጫ ላይ መሆናችንን ሲያስገነዝበን የዕብራውያን ጸሐፊ፥ እንግዲህ እነዚህን የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን፥ እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ ቶሎም የሚከበንን ኃጢአት አስወግደን፥ የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና። አለ፤ (ዕብ. 12፥1-2)።

ሁላችን ሯጮች ነን። ሕይወት ሩጫ ስለሆነ። አንዳንዶች በአጭሩ ይጨርሱታል። አንዳንዶች ዘለግ ይልባቸዋል፤ ወይም ይልላቸዋል። የአንዳንዶቹ ረዥም ነው።

የዕብራውያን ጸሐፊ፥ ‘እንሩጥ’ ይላል። ይህን ያለው በተለይ ለዕብራውያን አማኞችን ቢሆንም፥ በክርስቶስ ላመኑ ቅዱሳንም ሁሉ ነው። ቀደም ሲል በዕብ. 6፥1 ‘እንሂድ’ ብሎ ነበር፤ ስለዚህ የክርስቶስን ነገር መጀመሪያ የሚናገረውን ቃል ትተን ወደ ፍጻሜ እንሂድ። ወደ ግብ፥ ወደ ፍጻሜ ከሆነ መሄድም መሮጥም ጉዞ ነው።

በተለይ፥ ‘እንሩጥ’ ሲል ከፊታችን የሮጡትን ምስክር አድርጎ ነው። ብዙ ናቸው። እንደ ደመና የከበቡን እስኪመስሉ ብዙ ናቸው። በዕብ. 11 ጥቂቶቹ ብቻ ተጠቅሰዋል።

እንድንሮጥ የተነገረን ሁለት ነገሮችን እያደረግን ነው፤

  1. ከኃጢአት ጋር ወዳጅ ባለመሆን፤ ወይም ባላጋራ በመሆን። እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ ቶሎም የሚከበንን ኃጢአት አስወግደን፥ . . . እንሩጥ።
  2. ከፊታችን በጽድቅ ሮጦ የጨረሰውን እያየን። የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና።

ታላቁ ሩጫ ለምን ታላቁ ሩጫ እንደተባለ ባይገባኝም፥ ሁላችንም ሯጮች መሆናችንን አንርሳ። ስንሮጥም በእውነት እንሩጥ። በጽድቅ እንሩጥ። ለማሸነፍ ሳይሆን ለመጨረስ እንሩጥ።

The post ታላቅ ሩጫ first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ስለ ብሽሽቅና ፉክክር-ተኮር ስብከቶች ጥቂት ልበል! https://deqemezmur.com/2023/01/21/rivality-and-competition/ Sat, 21 Jan 2023 18:31:30 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2172                    በወንድም ጌታሁን ሄራሞ ተጻፈ በጸሃፊው ፈቃድ በዚህ ድረ ገጽ ወጥቷል፤     ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ ብቅ ያሉ አንዳንድ የ”Emerging Churches” አገልጋዮች የሚያምኑትን እውነት ለሌሎች ለማስተላለፍ እየሄዱበት ያለው አካሄድ ከወንጌል ማዳረስ ዓላማ ይልቅ ብሽሽቅና ፉክክር የነገሰበት ሆኖ አግኝቼዋለሁ። የወንጌል መልዕክት አውዳዊ ይዘቱን የጠበቀ መሆን እንዳለበት ከሐዋሪያው […]

The post ስለ ብሽሽቅና ፉክክር-ተኮር ስብከቶች ጥቂት ልበል! first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
                   በወንድም ጌታሁን ሄራሞ ተጻፈ በጸሃፊው ፈቃድ በዚህ ድረ ገጽ ወጥቷል፤
    ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ ብቅ ያሉ አንዳንድ የ”Emerging Churches” አገልጋዮች የሚያምኑትን እውነት ለሌሎች ለማስተላለፍ እየሄዱበት ያለው አካሄድ ከወንጌል ማዳረስ ዓላማ ይልቅ ብሽሽቅና ፉክክር የነገሰበት ሆኖ አግኝቼዋለሁ። የወንጌል መልዕክት አውዳዊ ይዘቱን የጠበቀ መሆን እንዳለበት ከሐዋሪያው ጳውሎስ የበለጠ ያስተማረን የለም። ይህን አውዳዊ የወንጌል ስብከት ጥበብን ግልፅ ለማድረግ በቀዳሚነት ወደ ሐዋ ሥራ ምዕራፍ 17 መዝለቅ ግድ ይላል።
     በክፍሉ ሐዋሪያ ጳውሎስ የግሪክ ዋና ከተማ ወደ ሆነችው ወደ አቴንስ በገባ ጊዜ መንፈሱ እንደተበሳጨበት በክፍሉ ተቀምጧል። ከአንድ እግዚአብሔር ውጭ ሌላ ጣዖት ሲመለክ የእግዚአብሔር መንፈስ ያደረበት ማንም ሰው መንፈሱ ይበሳጭበታል፤ እንዲያውም ግራ ሊገባን የሚገባውና ራሳችንን መፈተሽ ያለብን መንፈሳችን ባይበሳጭ ነው፤ ይህን እውነት መካድ አይቻልም።
ታዲያ ይህን የውስጥ ብስጭት አምቆ ይዞ የእውነት ወንጌልን በፍቅር ለሌሎች ለማድረስ ራስን የመግዛት መንፈስና ጥበብ ልንካን ይገባል። ለምሣሌ ሐዋሪያ ጳውሎስ በተበሳጨበት ልክ…የአቴና ሰዎች ሆይ እናንተ የምታመልኩት ጣዖት ነው፤ እንጨት ነው፤ ጣውላ ነው፤ ቁም ሳጥን ነው.. ወዘተ” እያለ ስብከቱን አልጀመረም። ሆኖም ሐዋሪያው የአቴና ሰዎች ከያዙት እምነት ውስጥ የጋራ እሴቶችን ፈለገ። ወደ አንድ መሠረታዊ እውነትም ደረሰ…የአቴና ሰዎች ቢያንስ በፈጣሪ መኖር ያምናሉ…They are not atheists! This shared spiritual value is a good starting point for his preaching. እናም የነርሱን ነባራዊ ሁኔታን “acknowledge” አድርጎ ስብከቱን ቀጠለ፦ “ጳውሎስም በአርዮስፋጎስ መካከል ቆሞ እንዲህ አለ። የአቴና ሰዎች ሆይ፥ እናንተ በሁሉ ነገር አማልክትን እጅግ እንደምትፈሩ እመለከታለሁ።” ቁ. 22 በመቀጠልም ሐዋሪያ ጳውሎስ ሌላ ሁለተኛ የጋራ መንፈሳዊ እሴት በእምነታቸው ውስጥ አገኘ፦” የተወሰኑትንም ዘመኖችና ለሚኖሩበት ስፍራ ዳርቻ መደበላቸው። ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም። ከእናንተ ከባለ ቅኔዎች አንዳንዶች ደግሞ እኛ ደግሞ ዘመዶቹ ነንና ብለው እንደ ተናገሩ፥ በእርሱ ሕያዋን ነንና እንንቀሳቀሳለን እንኖርማለን።” ቁ 28እንዲያውም እዚህ ጋ ሐዋሪያው ባለቅኔዎችን “እንደተናገሩ” እያለ “Quote” ሲያደርጋቸው እንመለከታለን። ደግሞም ባለቅኔዎቹ የእግዚአብሔር ዘመዶች ነን ማለታቸውን… እግዚአብሔር ከሰው ሩቅ አለመሆኑን…ለማስገንዘብ ሲጠቀም እናስተውላለን።ሆኖም ከላይ የጠቀስኩትን ሁለቱን እሴቶች ከጠቀሰ በኋላ ሐዋሪያው እውነትን በፍቅር እንዴት እንደገለፀ እንመልከት፦
” የምታመልኩትን እየተመለከትሁ ሳልፍ ለማይታወቅ አምላክ የሚል ጽሕፈት ያለበትን መሠዊያ ደግሞ አግኝቼአለሁና።እንግዲህ ይህን ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ እነግራችኋለሁ።ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ነውና እጅ በሠራው መቅደስ አይኖርም፤ እርሱም ሕይወትንና እስትንፋስን ሁሉንም ለሁሉ ይሰጣልና አንዳች እንደሚጎድለው በሰው እጅ አይገለገልም።” ቁ 23
       በዚህ በሐዋሪያ ጳውሎስ ማብራሪያ ውስጥ “ሳታውቁ የምታመልኩትን” የሚለውን አስምሩልኝ። ምን ማለት ነው? አምልኮ ዕውቀትን ይቀድማል? ወይስ ዕውቀት አምልኮን ይቀድማል? በእኔ አረዳድ የሰው ነፍስ የፈጣሪዋን እስትንፈስ ስላለባት ዕውቀት በሌለበትም ፈጣሪዋን ፍለጋ ትኳትናለች ስለዚህም ሐዋሪያው ጳውሎስ “ለማይታወቅ አምላክ” የሚለውን አባባላቸውን በጥበብ ወደ እውነተኛው አምላክ ለመጠቆም ተጠቅሞበታል…It is just as if writing the exact payable amount on a blank cheque paper! ሁለተኛውን የጳውሎስ ማስተካከያ ደግሞ በቁ 29 ተጠቅሷል። ” እንግዲህ የእግዚአብሔር ዘመዶች ከሆንን፥ አምላክ በሰው ብልሃትና አሳብ የተቀረጸውን ወርቅ ወይም ብር ወይም ድንጋይ እንዲመስል እናስብ ዘንድ አይገባንም።” እዚህ ጋ የጳውሎስ አመክንዮ ግልፅ ነው፤ የአመክንዮው መነሻው የራሳቸው እምነት ነው…እንግዲህ የእግዚአብሔር ዘመዶች ከሆንን…የሚለው! የጳውሎስ ጥያቄ… እንግዲህ በእናንተና በእግዚአብሔር መካከል ዝምድና ካለ እናንተ በእግዜር አምሳልም ከተፈጠራችሁ ከተቀረፀ ድንጋይ ወይም ወርቅ ጋር እንዴት ልትቆራኙ/ልትዛመዱ ቻላችሁ? የሚል ነው። በሌላ አነጋገር ዝምድናው ካለ “ዲ.ኤን. ኤ”ያችሁ በየትኛው አመክንዮ ወደ ድንጋይ ሄደ? ማለቱ ነው።
     እንግዲህ ከላይ ያለውን የአውዳዊ ስብከት ዘዴን ጠቅሰን ስንሞግት አንዳንዶቻችን መፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኢየሱስም በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 13 ላይ… ደንቆሮዎች፣ ዕውሮች፣እባቦች፣ የእፉኝት ልጆች፣ በውጭ በኖራ የተለሰነ መቃብር…ወዘተ” የሚሉ ኃይለ ቃሎችን ተጠቅሞ የለም ወይ? የሚል ጥያቄ ሊፈጠርብን ይችላል። ይህ የማቴዎስ 23 መልዕክት ለማን address እንደተደረገ ካለማወቅ የመነጨ ጥያቄ ነው። ቁጥር 13 እንደሚያመለክተው መልዕክቱ የተላለፈው ለግብዝ ፈሪሳውያንና ጻፎች እንጂ ለተራው ምዕመን አይደለም። ኢየሱስ በሌሎች የመፅሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም ግብዝ የሃይማኖት መሪዎችን ፊት ለፊት ነበር የሚጋፈጣቸው… ስብከቶቹና ትምህርቶቹ እንደእኛዎቹ ፈፅሞ ጅምላ ጨራሽ አይደሉም። ለምሣሌ በዮሐንስ ወንጌል ምዕ 4 ኢየሱስ ሴትዮው አመንዝራ መሆኗን እያወቀ እንኳን ተግባቦቱን የጀመረው “አንቺ ሴተኛ አዳሪና 5 ባሎች የነበሩሽ ነሽ” በማለት ሳይሆን “ውኃ አጠጪኝ” በሚል ልመና ነበር….እንዲሁም ነቢዩ ናታን ንጉሥ ዳዊት በዝሙት ኃጢአት መውደቁን ካወቀ በኋላ በቀጣይነት ለመልዕክቱ ሜቴዶሎጂ የፀለየ ይመስለኛል…መልዕክት መቀበል አንድ ነገር ነው…የተቀበልነው መልዕክት እንዴት ይተላለፍ?…የሚለው ጥያቄ ሌላው ቀጣይ የቤት ሥራ ነው። ደግሞም ለዳዊት መልዕክት ማስተላለፍና ለሌላ መደበኛ እሥራኤላዊ መልዕክት ማስተላለፍ ሜቶዶሎጂው ለየቅል ነው። እናም ናታን በጣም “poetic” በሆነ መልኩ ነበር ዳዊትን በግለ-ሂስ (self-criticism) ቅርቃር ውስጥ ያስገባው(2ኛ ሳሙ ምዕ 12)። በነገራችን ላይ ስህተትን ከማረም አኳያ ከሁሉም በላይ ስኬታማ ተግባቦት የሚባለው ሰዎች ራሳቸውን criticize እንዲያደርጉ የሚያስችለው ሜቶዶሎጂ ነው…ልክ ነቢዩ ናታን ዳዊት በራሱ ላይ እንዲፈርድ ያደረገበትና ኢየሱስም ከላይ የጠቀስኳት ሴት “ባል የለኝም” በማለት በራሷ “confess” እንድታደርግ ያስቻለበትን መንገድ ማለቴ ነው።
         በእኔ አተያይ ኢየሱስ በኃይለ ቃል ግብዞችን የገሰፀበትን ግሳፄ ለግብዞች “forward” ማድረግ እንችል ይሆናል፤ ነገር ግን “forward” ከማድረግ ባለፈ ኢየሱስም ይሁን ቀደምት ሐዋሪያትና ነቢያት(መጥምቁ ዮሐንስን ጨምሮ) ግብዞችን በገሰፁበት ልክ መገሰፅ የምንችልበት “Authority” ይኖረን እንደሆነ ለኔ ግልፅ አይደለም(እሱን ለሥነ መለኮት ምሁራን ልተዋው)። ስለዚህም አሁን በአንዳንድ “Emerging Churches” እየተስተዋሉ ያሉ ጅምላ ጨራሽና አውድ-አልባ የቃላት ብሽሽቆች ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው የሚያመዝን ነው። በአቴናው በሐዋሪያው ጳውሎስ አውድ-ተኮር መልዕክት ንስሐ የገቡ የአቴና ሰዎች አሉ፤ የቀሩትም ስብከቱን እንደገና ለመስማት ለጳውሎስ ቀጠሮ ሰጥተውታል(የሐዋ ሥራ 17፤34)። በተቃራኒው ጅምላ ጨራሽ ብሽሽቅና ከወንጌል ስብከት ጥበብ የፀዳ የስብከት ዘዴ የቱን ያህል ውጤት እንደሚያስገኝ መገመት ያን ያህል አያዳግትም።
      በነገራችን ላይ የነዚህ ቡድኖች ጮክ ብሎ ብሽሽቁን ማጧጧፋቸው ሌላም ድምፀት አለው። “ነባርና ዕድሜ-ጠገብ የፕሮቴስታንት ቤ/ክርስቲያናት ለዓመታት በፍርሃት ተሸብበው ያልሰበኩትን ወንጌል እኛ አዳዲሶቹ ዛሬ አሃዱ ብለን ደፍረን አጥር ጥሰን እየሰበክን ነው” የሚል በትዕቢት የተሞላ ድምፀት! ሆኖም ነባር የፕሮቴስታንት ቤተክርስቲያናት ቀደም ሲል ለወንጌል ዋጋ የከፈሉት እንደነሱ በተንቆጠቆጡ ቪላዎች እየኖሩና ቅንጡ መኪናዎችን እያሽከረከሩ ሳይሆን መስዋዕትነትን መክፈል አስፈላጊ በሆነበት ቅፅበት ሁሉ በወህኒ ቤት እየማቀቁ እንደነበር ማን በነገራቸው? ዛሬ የወቅቱን የፖለቲካ አውድ በዘዴ ፈትሾ ለወንጌል መስዋዕትነት ለመክፈል የተዘጋጁ የሚመስሉ “opportunists” ስልትና ስሌት እንኳን ከእግዜሩ ከሰውም የተሰወረ አይደለም። አባቶቻችን ለወንጌል ዋጋን የከፈሉት ወንጌል ተቋማዊ በሆነ መልኩ በመንግስት ተቃውሞ በደረሰበት ዘመን እንጂ እንደ ዛሬዎቹ የወቅቱን የመንግስት መዋቅርና ሕገመንግሥት አቋም አስልተው አልነበረም።
በመጨረሻም እነዚህን “Emerging Churches” ያቀፈ አንድ ካውንስል አለ መሰለኝ። ይህ ካውንስል አቅሙና ብቃቱ ካለው ለግለሰቦቹ ከብሽሽቅና አጉል ፉክክር የፀዳ አውድ-ተኮር ወንጌል እንዴት በጥበብ እንደሚሰበክ ሥልጠና ቢሰጣቸው መልካም ነው እላለሁ።

The post ስለ ብሽሽቅና ፉክክር-ተኮር ስብከቶች ጥቂት ልበል! first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች ነን? እንዴት? የእግዚአብሔር ልጆችስ ነን? እንዴት? https://deqemezmur.com/2022/10/28/%e1%8b%a8%e1%88%98%e1%88%88%e1%8a%ae%e1%89%b5-%e1%89%a3%e1%88%95%e1%88%ad%e1%8b%ad-%e1%89%b0%e1%8a%ab%e1%8d%8b%e1%8b%ae%e1%89%bd-%e1%8a%90%e1%8a%95-%e1%8a%a5%e1%8a%95%e1%8b%b4%e1%89%b5-%e1%8b%a8/ Fri, 28 Oct 2022 23:30:53 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2163   የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት ጥቅስ በ2ጴጥ. 1፥4 የሚገኘው ነው። ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን። 2ጴጥ. 1፥4 መጀመሪያ ያልሆንነውን ነገር እናስተውል። እኛ መለኮት አይደለንም። መለኮት አንድ ብቻ ነው። እኛ አማልክት አይደለንም። እኛ በምድር ላይ ውር ውር የምንል ትንንሽ እግዚአብሔሮች […]

The post የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች ነን? እንዴት? የእግዚአብሔር ልጆችስ ነን? እንዴት? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
 

የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት ጥቅስ በ2ጴጥ. 1፥4 የሚገኘው ነው። ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን። 2ጴጥ. 1፥4

መጀመሪያ ያልሆንነውን ነገር እናስተውል።

  1. እኛ መለኮት አይደለንም። መለኮት አንድ ብቻ ነው። እኛ አማልክት አይደለንም። እኛ በምድር ላይ ውር ውር የምንል ትንንሽ እግዚአብሔሮች አይደለንም። መዝ. 82፥6 ላይ የሚገኘው፥ እኔ ግን፦ አማልክት ናችሁ፥ ሁላችሁም የልዑል ልጆች ናችሁ፤ የሚለው ቃል ስለ አምላክ ሳይሆን ስለ ሰዎች እንደሚናገር ቀጥሎ ቁጥር 7 ላይ ያለው፥ ነገር ግን እንደ ሰው ትሞታላችሁ፥ ከአለቆችም እንደ አንዱ ትወድቃላችሁ አልሁ። የሚለው ቃል ይመሰክራል። አምላክ አይሞትምና እነዚህ ከሞቱ ቃሉ ስለ መለኮት አለመናገሩ መሆኑን እናውቃለን። ጌታም በዮሐ. 10፥34 ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፦ እኔ፦ አማልክት ናችሁ አልሁ ተብሎ በሕጋችሁ የተጻፈ አይደለምን? ብሎ ሲጠቅስ ያንኑ አሳብ መግለጡ ነው። ቃሉ ኃያላን፥ ክቡራን ማለት ነው። ‘እነዚያ እንኳ እንደዚያ ከተባሉ፥ እኔ ከአብ የመጣሁት ያንን ብል ተገቢ ነው።’ ማለቱ ነው።
  2. እኛ በፍጥረታችን የመለኮት ባሕርይ የለንም። ስንፈጠር ሰዎች ነን እንጂ አማልክት ወይም መናፍስት አይደለንም። ሕይወት ያለን፥ የሕይወት እስትንፋስ እፍ የተባለብን፥ ሕያዋን ወይም ከተፈጠርንባት ቅጽበት ጀምሮ ዘላለማውያን የሆንን ሰዎች ነን። ይህ ስለ አዳምም ስለ እኛም፥ ወይም በአዳም በኩል ስለ እኛም ነው።
  3. የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት በምንም መልክ የክርስቶስ እኩዮች ወይም አቻዎች አያደርገንም። ክርስቶስ እግዚአብሔር ነው፤ ወይም ከሥላሴ አካላት አንዱ ነው። እኛ ግን ፍጡራን እና ፍጡራን ብቻ ነን።
  4. የኛ ልጅነት ከክርስቶስ ልጅነት በሁሉ ረገድ፥ በመልኩም፥ በዓይነቱም፥ በደረጃውም የተለየ ልጅነት ነው። ግን ልጅነት ነው። እኛ ልጆች የተደረግን ልጆች ነን። ጌታ፥ ‘አባቴና አባታችሁ’ ሲል ይህንን ያሳያል። ‘አባታችን’ አላለም። “‘አባቴና አባታችሁ’ ሲል ያው አባት አንድ መሆኑን መናገሩ ነው፤ አይደል?” ሊባል ይቻላል። ልክ ነው፤ አባት አንድ ነው፤ አባትነቱ ግን የተለያየ ነው። ‘አባታችን ሆይ’ ብለን እንጸልይ የል?’ ሊባል ይቻላል። አዎን፤ ግን፥ ‘ብላችሁ ጸልዩ’ ነው ያለው። እዚያው ያንን ባስተማረበት ክፍል ውስጥ፥ ‘የሰማዩ አባታችሁ’ እያለም አስተምሯል፤ ‘የሰማዩ አባታችን’ አላለም። ለአይሁድ አባታችን እያለ ሳይሆን አባቴ እያለ መናገሩ ምን ማለቱ እንደሆነ፥ በግልጽ ራሱን ከአብ ጋር ማስተካከሉ እንደሆነ ገብቷቸዋል። ሊወግሩት የቃጡት አሳልፈውም የሰጡት ስለዚህ ነው። ይሁን እንጂ ልጆች ሆነናል፤ በመደረግ።
  5. እኛ ከፍጥረታችን ወይም በተፈጥሮአችን የአዳም፥ የወደቀው አዳም ልጆች ነን። በእነዚህም ልጆች መካከል እኛ ሁላችን ደግሞ፥ የሥጋችንንና የልቡናችንን ፈቃድ እያደረግን፥ በሥጋችን ምኞት በፊት እንኖር ነበርን እንደ ሌሎቹም ደግሞ ከፍጥረታችን የቁጣ ልጆች ነበርን። ኤፌ. 2፥3። እነዚያ ‘የአብርሃም ልጆች ነን’ እያሉ ለሚኩራሩት የአብርሃም ሳይሆን የዲያብሎስ ልጆች መሆናቸውን በግልጽ ነበር የነገራቸው፤ ዮሐ. 8፥39-44።

1ኛ፥ ልጆች ነን።
ልጅ የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰፊ ትርጉም ያለው ቃል ነው። የሥጋ ልጅ ልጅ ነው፤ ልጅ ናት። በቀጥታ ከወላጅ የተወለደም፥ በቀጥታ ሳይሆን የልጅ ልጅ የሆነም፥ ዘር የሆነም ልጅ እየተባለ ተጠርቶአል። ሁለቱ የዮሴፍ ልጆች፥ ለምሳሌ፥ የያዕቆብ ልጆች ተብለው ከ12ቱ ነገድ ጋርም ተቆጥረዋል። በሥጋ ያልተወለዱም ልጆች ተብለዋል፤ ያም ባሕርይን ገላጭ አሳብ ነው፤ የሚያስተራርቁ የእግዚአብሔር ልጆች ተብለዋል፤ የእፉኝት ልጆች፥ የቁጣ ልጆች፥ የዲያብሎስ ልጆች ሲል በሥጋ መወለድን መናገሩ አይደለም። ምስስልን መናገሩ ነው። ምሳሌያዊና ባሕርያዊ ልጅነቶችም አሉ፤ ለምሳሌ፥ የነጎድጓድ ልጆች፥ እና የመሰሉትን አላወሳሁም።ልጅነት የግንኙነት ገላጭ ነው። በቀጥታ ብንወለድም ግንኙነት አለ፤ ልደቱ ወይም ልጅነቱ አካላዊ ባይሆንም ወይም ካልሆነም ግንኙነቱ ግን አለ። እስራኤል የእግዚአብሔር ልጅ ወይም በኵር ልጅ ሲባሉ የግንኙነት ጉዳይ የተሰመረበት ነው። ከአብርሃም ጋር የተገባ ኪዳንና ግንኙነት አለና፥ በጠቅላላው እንደ ሕዝብ ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸው ግንኙነት ማዕከላዊው ቦታ ላይ የሚገኝ ነው።እኛ የእግዚአብሔር ልጆች የመሆናችን እውነት በግልጽ የተጻፈ ቃል ነው። መጽሐፍ ቅዱስ እኛ በጌታ የሆንን ቅዱሳን የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ምንም ሳይንተባተብ ይነግረናል። የእግዚአብሔር ልጆች ነን። ይህን ግልጽ ነው። ልጆች ነን።ግን እንዴት ልጆች ሆንን? ይህ ትልቅ ጥያቄ ነው። የልጅነታችን ሂደትስ እንዴት ነው የተከናወነው? ልጆች የሆንንበት መንገድ ደግሞ አለ፤ ልጆች የሆንንበትን መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ በገላጭ ቃላት ይገልጠዋል።

ሀ፥ ስጦታ፤ ልጅነት ስጦታ ነው። ልጅነት ስጦታችን ነው። ስጦታ ይለዋል። ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤ ዮሐ. 1፥12። ክርስቶስን ስንቀበለው የእግዚአብሔር ልጆች እንሆናለን። ሰጣቸው ሲል የተሰጠ ሥልጣን መሆኑ ይታያል። የተሰጠን፥ የተቀበልነው ሥልጣን ነው። ቀድሞ እኛ ልጆች አልነበርንም፤ ሥልጣኑም አልነበረንም። ኋላ ግን ተሰጠንና ኖረን፤ እኛም ልጆች ሆንን።ይህ ስጦታ የተሰጠን በእምነት በኩል፥ ክርስቶስን በመቀበል ነው፤ በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤ ገላ. 3፥26። ስጦታ ከሆነ የተሰጠን ነን ማለት ነው። የተቀበልን ከሆንን የሰጠን አለ ማለት ነው። የተሰጠን ሆነን እንዳልተሰጠንና እንደተቀዳጀነው ሆነን የምንኮፈስበት ምንም ምክንያት ሊኖረን አንችልምም፥ የተገባም አይደለም። አስቀድመን የእግዚአብሔር ልጆች ያልነበርን የቁጣ ልጆች ነበርን፤ በእነዚህም ልጆች መካከል እኛ ሁላችን ደግሞ፥ የሥጋችንንና የልቡናችንን ፈቃድ እያደረግን፥ በሥጋችን ምኞት በፊት እንኖር ነበርን እንደ ሌሎቹም ደግሞ ከፍጥረታችን የቁጣ ልጆች ነበርን። ኤፌ. 2፥3።

ልጅነት እውነት ነው፤ ልጅነታችን እርግጥ ነው። እርሱም በፍቅር የተሰጠንና በትሕትና የተቀበልነው ስጦታ ነው። የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን እዩ፥ እንዲሁም ነን። ስለዚህ ምክንያት ዓለም እርሱን ስላላወቀው እኛን አያውቀንም። ወዳጆች ሆይ፥ አሁን የእግዚአብሔር ልጆች ነን፥ ምንም እንደምንሆን ገና አልተገለጠም። ዳሩ ግን ቢገለጥ እርሱ እንዳለ እናየዋለንና እርሱን እንድንመስል እናውቃለን። 1ዮሐ. 3፥1-2። ልጅነታችን በፍቅር የተሰጠንና የተቀበልነው ስጦታ ነው። ስጦታ ሽልማት አይደለም። ሽልማት በሆነ ነገር በልጠን፥ ልቀን የምናገኘው የኛ ሥራ ያለበት የሌሎችን አድናቆት የምናገኝበት የሥራ ፍሬ ነው። ይህ የኛ ልጅነት ድንቅና ግሩምም ነው። ግንኙነት ነው፤ ሥልጣን አለበት፤ ወራሽነትም ነው። ይህም ሁሉ ሆኖ ግን ስጦታና ስጦታ ብቻ ነው። ስጦታ ከሆነ ሰጪ አለ፤ ተቀባይ አለ። እኛ ተቀባዮች ብቻ ነን።

ለ፥ ዳግም ልደት፤ ልጅነታችንን ገላጭ የሆነው ሌላ ቃል ዳግም ልደት ወይም መንፈሳዊ ልደት ነው። ይህ ማለት መንፈሳችን ለብቻው ዳግም ተወልዶ ነፍሳችንና ሥጋችን ደግሞ በዝግመትና በትንሣኤ ዳግም ይወለዳሉ ማለት አይደለም። እኛ ኋላ የምንገጣጠም ቁርጥራጮች አይደለንም። መጽሐፍ ቅዱስ ሁለንተናችንን ሰው ብሎ ይጠራዋል። ኢየሱስም መልሶ፦ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው። . . . ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል ስላልሁህ አታድንቅ። ዮሐ. 3፥3 እና 7። ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር ነው ያለው። ዳግም መወለድን ከመንፈስ መወለድም ይለዋል፤ ቁጥር 5። ዳግመኛ መወለድን ከማይጠፋ ዘር በእግዚአብሔር ቃል መሆኑንም ይነግረናል፤ ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም፥ በሕያውና ለዘላለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ። 1ጴጥ. 1፥23። እዚህ ዘር የተባለው ቃሉ ራሱ ነው። ይህ ዘር ቃሉ መሆኑን የምናገኘው ከቀጣዮቹ ሁለት ጥቅሶች (ከቁ. 24-25) ነው። ይህ ዳግመኛ መወለድ እንደገና መወለድ ነው። እዚሁ 1ጴጥ. 1፥3-4 ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፥ እድፈትም ለሌለበት፥ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ፤ ይላል። በሥጋ ስንወለድ የወላጆቻችን ልጆች እንደምንሆን እንደገና ወይም ዳግመኛ ስንወለድ የእግዚአብሔር ልጆች እንሆናለን። ይህ ልደት የመንፈስ ልደት ወይም መንፈሳዊ ልጅነት ነው። እግዚአብሔር መንፈስ ነው። የእግዚአብሔር ልጅ መሆን መንፈስ መሆን አይደለም። በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት መወለድና የእግዚአብሔር ልጆች መሆን ነው። አባ አባት ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና። ሮሜ. 8፥15። እዚህ ጥቅስ ውስጥም፥ ልጅነትን ወይም የልጅነት መንፈስን መቀበላችንን ይነግረናል። መቀበል ከኖረ ሰጪ አለ። መቀበል ከኖረ፥ ከመቀበል በፊት ያ ነገር በእኛ ዘንድ ያልነበረ ነገርና ኋላ የኖረ ነገር ነው።

ሐ፥ ሦስተኛው ልጆች መደረጋችን ነው።
ሦስተኛው ልጆች የመሆናችን ገላጭ ቃል ልጆች የመደረጋችን እውነት ነው። ቃሉን ከወደድን ማደጎ እንበለው፤ ከፈለግን ጉዲፈቻ እንበለው፤ ከፈለግን የእንግሊዝኛውን ወስደን adoption እንበለው፤ ቃሉ ቢጥመንም ባይጥመንም አሳቡ ግን ያ ነው። ይህንን ቃል በአዲስ ኪዳን በጳውሎስ ተደጋግሞ ተጽፎ እናገኘዋለን። ይህ የግሪክ ቃል υἱοθεσία ሁዮቴሲያ የተባለው ነው። ትርጉሙ ልጅ መደረግ፥ እንደ ልጅ መደረግ፥ ልጅ ተደርጎ መወሰድ ማለት ነው። በአዲስ ኪዳን ቃሉ በተጻፈባቸው ቦታዎች ሁሉ በጳውሎስ ነው የተጠቀሰው። ይህ ጳውሎስ ልጆች መሆናችንን አበክሮ የጻፈ ሐዋርያም ነው። እና ልጆች መሆናችንን ሲናገር ይህን ቃል መጠቀሙ በመንፈስ ቅዱስ በመመራት እንጂ ባለማወቅ ወይ በመሰለኝ አይደለም። ልጅ መሆንና ልጅ መደረግ የሚጋጩ ሁለት ነገሮች አይደሉም። ሁለት የልጅነት እርከኖች ወይም ደረጃዎችም አይደሉም። ሁለቱም አንድ ልጅነት ናቸው።

ዳግም ልደት በሥጋ ከወላጆቻችን እንደተወለድነው፥ በዮሐ. 3 ጌታ ለኒቆዲሞስ እንዳብራራው፥ በመንፈስ ወይም በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት መንፈሳዊው ማንነታችን የእግዚአብሔር ልጅ ሲሆን ነው። ይህ ማለት ቀድሞ በአካላዊ ሕይወት ኖረንም ልጆች አልነበርንም ማለት ነው። በቲቶ 3፥5 እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፥ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለ ነበረው ሥራ አይደለም፤ ይላል። እዚህ አዲስ ልደት (παλιγγενεσία) እንደገና መወለድ ነው። ቃሉ እዚህና ማቴ 19፥28 ብቻ የሚገኝ አዲስነትን ገላጭ ነው። ዳግም ስንወለድ አንዲስ ፍጥረት ነው የምንሆነው፤ ስለዚህ ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፎአል፤ እነሆ፥ ሁሉም አዲስ ሆኖአል። 2ቆሮ. 5፥17። ዳግም ልደት እና ልጅ መደረግ ያው አንዱ ነገር ነው በተለያዩ መግለጫ ቃላት የተገለጠው እንጂ ሁለት እርከኖች ወይም ደረጃዎች አለመሆናቸውን ደግመን እናስብ።

ልጅ መደረግ ለሚለው ቃል ጳውሎስ የጻፋቸው ጥቅሶች እነዚህ ናቸው፤

አባ አባት ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና። ሮሜ 8፥15።

እርሱም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን የመንፈስ በኵራት ያለን ራሳችን ደግሞ የሰውነታችን ቤዛ የሆነውን ልጅነት እየተጠባበቅን ራሳችን በውስጣችን እንቃትታለን። ሮሜ. 8፥23።

እነርሱ እስራኤላውያን ናቸውና፥ ልጅነትና ክብር ኪዳንም የሕግም መሰጠት የመቅደስም ሥርዓት የተስፋውም ቃላት ለእነርሱ ናቸውና፤ ሮሜ. 9፥4።

ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤ እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ፥ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ። ገላ. 4፥4-5።

በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን። ኤፌ. 1፥5።

እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ነን። የሆንነው ደግሞ በመደረግ ነው። ተደርገን ነው። ማለትም፥ እግዚአብሔር ወድዶ ልጆቹ አድርጎን ነው። በፍጥረታችን ወይም በአፈጣጠራችን ልጆች አልነበርንም። እግዚአብሔር ግን ልጆቹ እንድንሆን ወደደና ልጆቹ አደረገን፤ እንደ ልጆቹ አድርጎ ተቀበለን። ልጅነት የተፈጥሮ መብታችን አይደለም። ከተደረግን በኋላ ግን፥ ይህ ልጅነት ከተሰጠን በኋላ ግን፥ ልጅነት መብት ብቻ ሳይሆን ሥልጣንም ሆነ። ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤ ዮሐ. 1፥12። የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ስናስብና ስንደሰትበት፥ ልጆች የተደረግን መሆናችንንም አንዘንጋ። ልጆች የተደረግን ልጆች ነን።

በነገረ መለኮት፥ በተለይም በነገረ ክርስቶስ እና በነገረ ሰብዕ፥ የባሕርይ ልጅ እና የጸጋ ልጅ ሲባል ሰምተን እናውቅ ይሆናል። (የባሕርይ ተካፋይ ስለሚለው አሳብ ለብቻ እመለሳለሁ።) የባሕርይ ልጅ ሲባል ከአድራጊው ጋር አንድ መሆንን አመልካች ነው። ይህ ለኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅነት የምንጠቀምበት የስነ መለኮት ቃል ወይም ሐረግ ነው። (እዚህ ላይ፥ የጳውሎስ ፈቃዱን የእግዚአብሔር ልጅ መጽሐፍ በጠቅላላው፥ በተለይ የኛን ልጅነት በተመለከተ ደግሞ በምዕራፍ 8 እና 9ን ተንትኖታልና፥ ይህንን እንድታነብቡ፥ እንድታነብቡ ብቻ ሳይሆን እንድታጠኑ፥ አደራ እላለሁ።) ባሕርይ የሚለውን ቃል ተፈጥሮ እንዳንለው ኢየሱስ ፍጡር አይደለምና የተፈጥሮ ልጅ አይባልም። (ሆኖም፥ አዲስ ኪዳን ይህንን ቃል በአንዳንድ ጥቅሶች ውስጥ ተፈጥሮም ይለዋል።) ሥሪት እንዳይባልም እርሱ ሠሪ እንጂ ተሠሪ አይደለምና ይህም አያስኬድም።

የባሕርይ ልጅ መሰኘቱ ወልድ እና አብ አንድ ባሕርይ ወይም በእንግሊዝኛ essence በግሪክ οὐσία ወይም ούσιος የተባለውን መሆናቸውን ነው። የኒቅያው ጉባኤ አብ እና ወልድ አንድ ባሕርይ ὁμοούσιος ሆሞኡሲዮስ ወይም ὁμοούσιον ሆኖኡሲዮን ያለው ያንን ነው። አብ የሆነውን ሁሉ ወልድም ነው፤ ኹነታችው በሁሉ አንድ ነው። በዚህ ረገድ እግዚአብሔርን የሚመስል እግዚአብሔር ብቻ ነው። አብ፥ ወልድ፥ መንፈስ ቅዱስ በባሕርይ አንድ ናቸው። እግዚአብሔርን በዚህ ማንነቱ ከፍጥረት ወይም ከፍጡር የሚመስለው ምንም፥ ማንም የለም። ሰውን በመልኩና በምሳሌው መፍጠሩም ሰውን የመለኮት ባሕርይ አያላብሰውም ወይም አያቀዳጀውም። ሰው ሲፈጠር ሰው እንጂ፥ የተሰጠው ሥልጣን አለው እንጂ አምላክነት የለውም። መንፈሳዊነት አለው እንጂ መንፈስ አይደለም።

እግዚአብሔር መንፈስ ነውና መልክና አምሳል ሲባል እንደ አካል መልክ አድርገን መውሰድ የለብንም። ይህ መልክና ምሳሌ ምንም አካላዊነት የለበትም። መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔርን በሰውኛ አኳኋን ቢገልጠውም የሰው ዓይነት አይደለም። ስንዝር፥ ዓይኖች፥ ክንድ፥ ጀርባ፥ መሳቅ፥ መጸጸት፥ ወዘተ፥ በመሰሉ ቃላት ቢገልጠውም፥ ይህ ለሰው መረዳት ቃሉ የተጠቀመበት አገላለጥ ነው፤ anthropomorphism ይባላል፤ ስብዕናን ማላበስ ይባላል። ይህ ለእግዚአብሔር ብቻ ሳይሆን ለግዑዛን ነገሮችም ይደረጋል። ወንዞች ሲያጨበጭቡ፥ ተራሮች ሲዘልሉ፥ ፀሐይ እንደ አርበኛ ሲወይም ሮጥ ወዘተ፥ የዚህ ዘር ነው።

እኛ በባሕርይ፥ በፍጥረት፥ ወይም በሥሪት የምንመሳሰለው ከአዳም ጋር ነው፤ በቀጥታ ልጁ የምንሆነውም የአዳምን ነው። ከአዳም ጋር ፍጹም አንድ ነን። በኃጢአት ከመውደቃቸው በፊት ከነበራቸው ንጽሕና በቀር አንድ ነን። አዳም ሲፈጠር ሰው እንጂ አምላክ አልነበረም። ሰው እንጂ መንፈስም አልነበረም። ፍጡር እንጂ ልጅም አልነበረም። እኛም ቀድሞ ልጆች አልነበርንም። በሆነ ጊዜ ግን ሆነን ተገኘን። በራሳችን አልሆንንም፤ ግን ተደረግን። ከላይ እንዳልኩት፥ ቃሉን ማደጎ እንበለው፥ ጉዲፈቻ፤ ወይም የእንግሊዝኛውን adoption እንውሰድ ወይም በሌላ በምናውቃቸው ቋንቋዎች እንጥራው ነጥቡ ልጆች ያልነበርን እኛ ልጆች #መደረጋችን፥ እንደ ልጆች መሆናችን፥ ልጆች መሆናችን ነው።

እኛ ቀድሞ ወገን አልነበርንም፤ ኋላ ግን ወገን ሆንን፤ ምሕረት ያገኘን አልነበርንም፤ ምሕረት ያገኘን ሆንን። እናንተ ቀድሞ ወገን አልነበራችሁም አሁን ግን የእግዚአብሔር ወገን ናችሁ፤ እናንተ ምሕረት ያገኛችሁ አልነበራችሁም አሁን ግን ምሕረትን አግኝታችኋል። 1ጴጥ. 2፥10። ወገን ያልነበርነው ወገን ከሆንን፥ ተደረግን ማለት ነው። ቀድሞም ወገን የነበረ ሰው ወገን አይደረግም። ለምሳሌ፥ ለአጎቶቼ እኔ የወንድማቸው ወይም የእኅታቸው ልጅ ነኝ። ስወለድ ጀምሮም ወገን፥ ዘመድ ነኝ። ሊያደርጉኝ አይችሉም ቀድሞም ነኝና። ያልሆነ፥ ያልነበረ ሲደረግ ግን ያ ሌላ ነገር ነው። ደግሞም ይቻላል። በተለያዩ ባህሎች አንድ ወይ ሌላ ሥርዓት ይፈጸምና ዝምድና ይፈጠራል። ይህ የጋብቻ ዝምድናን አይጨምርም። አንድ ምሳሌ ብንወስድ፥ በአገራችን የጡት ልጅ የሚባል ልጅነት አለ። በሥርዓቱ ጡት ሳይሆን ጣት ነው የሚጠቡት። ግን አንድ ጡት ጠብተው ያደጉ ወንድማማች ወይም ወንድምና እኅት ይሆናሉ። በአንዳንድ ባህሎች ጣትና ጣት ተበጥቶ ደም ይደማና ደምና ደም ተነካክተው የሥጋና ደም ዘመድ ሆኑ ይባላል። እነዚህ ልጅ ወይም ዘመድ ያልሆኑ ወገን ሲደረጉ ነው። ጉዲፈቻ ከነዚህ ዓይነቶቹ አንዱ ወገንነቶች ወይም ልጅነቶች ነው።

እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ከመሆናችን በፊት ልጆች አልነበርንም። ሳንሆን ኖረን፥ ስንሆን ያልነበርነውን ነው የሆንነው። ልጅ ነው የሆንነው። የሆንነውም በመደረግ ነው። ልጅነት ማንነታችን ነው። መደረግ ደግሞ የተደረግንበት መንገድ ነው። በብሉይ ኪዳን ልጆች ሳይሆኑ እንደ ልጅ መቆጠርም ልጆች ሆነው እንደ ሌላ ልጅ መቆጠርም አለ። ለሁለቱም አንድ አንድ ምሳሌ ላሳይ፤ ኤፍሬምና ምናሴ የዮሴፍ ልጆች ናቸው፤ ያዕቆብ ግን እንደ ራሱ ልጆች አድርጎ ወሰዳቸውና ከ12ቱ ነገድ ጋር ተቆጠሩ፤ ዘፍ. 48፥5-6። ልጅ ሆኖ ስላለመሆን ምሳሌ ደግሞ፥ በብሉይ ኪዳን የዋርሳ ሕግ የሚባል አለ። ባል ሳይወልድ ከሞተ የባል ወንድም ሚስቲቱን የራሱ አድርጎ ይወስዳል። ቢወልድም ልጆቹ ወይም ልጁ በሞተው ስም ይጠራል፤ የሟቹ ስምና ርስትም አይቋረጥም፤ ዘዳ. 25። ልጅ ሆኖ ልጅ አለመሆንም፥ ልጅ ሳይሆኑ ልጅ መሆንም አለ።

ጴጥሮስ በ1ጴጥ. 2፥10 ወገን ሳይሆኑ ወገን መሆንን የጠቀሰው ከሆሴዕ ትንቢት (ሆሴ. 1-2) የተወሰደ አስገራሚ የፈረሰና የታደሰ ግንኙነት ምስልም ታሪክም ነው። ይህ የኛ ወገንነትም ምስል ሆኖ በአዲስ ኪዳን በጴጥሮስ የተጠቀሰው ነው። የኛ ታሪክ የኛ ልጅነት ነው። የኛ ልጅነት ድንቅና ግሩም ነው። የኛ ልጅነት ሥልጣን ነው፤ ወራሽነትም ነው። ከእግዚአብሔር ጋር በክርስቶስ በኩል የተመሠረተ ግንኙነት ነው። ይህም ሁሉ ሆኖ ግን ልጅነታችን በበጎነቱ የተሰጠን፥ የተቀበልነው ስጦታና ስጦታ ብቻ ነው እንጂ የተቀዳጀነው ድልና መብት አይደለም። አንዳንድ የሐሰት አስተማሪዎች ይህንን እኛ በበጎነቱ ልጆች የተደረግንበትን ቸርነት ከክርስቶስ ልጅነት ጋር እያነጻጸሩ፥ የኛ ልጅነት እና የእርሱ ልጅነት የመንትያ ያህል አንድ እንደሆነ ሲናገሩና የሰዎችን እምነት ሲገለብጡ ማየት ምንኛ አሳዛኝ ነው!

ቀድሞ አባታችን ያልሆነ አባት የሌላው ልጆች የነበርነውን ልጆች አድርጎ ከተቀበለን የምን ልጅ ትባላለህ? የባሕርይ ልጅ አይደለንም። የባሕርይ ልጅ የሚባል ስለኛ የተነገረ ቃል ከቶም የለም። 1ጴጥ. 1፥4 የባሕርይ ተካፋዮች እንድንሆን በተስፋ ቃል መደረጋችንን ይናገራል። ይህንን በቀጣዩ እንመለከታለን።

  1. የባሕርይ ተካፋዮች

የልጅነታችን ሂደትስ እንዴት ነው የተከናወነው? የእግዚአብሔር ልጆች የሆንነው በተፈጥሮአችን ወይም በፍጥረታችን ሳይሆን እግዚአብሔር እንደ ልጆች አድርጎ ተቀብሎን ነው። ልጅነት የተሰጠን ስጦታ ነው እንጂ ከወላጆቻችን ስንወለድ በተፈጥሮ እንዳገኘነው ያለ መወለድ አይደለም። ቀደም ሲል ካየናቸው ጥቅሶች አንዱ በገላ. 4 የሚገኘው ነው። ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤ እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ፥ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ። ልጆችም ስለ ሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮኽ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ። ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ። ገላ. 4፥4-7።

ይህ ጥቅስ እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ እና ልጆች እንደሆንን በግልጽ ይናገራል። የእግዚአብሔር ቃል በማያሻማ መንገድ ልጆች መሆናችንን ይመሰክራል። ልጆች ነን። ልጆች የሆንነው ደግሞ ምንም የራሳችን ፍሬ ኖሮን ሳይሆን እግዚአብሔር ልጁን እንዲዋጀን ልኮት በእርሱ የዎጆ ሥራ በኩል ነው ልጆች የሆንነው። እርሱን ስንቀበል ልጆች ሆንን። ልጆች የሆንነው እግዚአብሔር ልጆቹ አድርጎን ነው። እንጂ በልጁ በኩል ከራሱ ጋር ባያስታርቀን ኖሮ፥ በራሳችንማ ጠላቶች ነበርን። ቃሉ ልጆች መሆናችንንም ልጆች የሆንነው በመደረግ መሆኑንም ይነግረናል። እነዚህ ሁለቱ እርስ በርስ የሚጋጩ አይደሉም።

ልጆች የሆንነው ልጆች ተደርገን ተወስደን ነው። ከሆንን እና ከተደረግን፥ አድርጎ የወሰደን አለ ማለት ነው። ልንሆን ተወስነን ከሆነ የወሰነ አለ ማለት ነው። በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን። ኤፌ. 1፥5። ይህ ቃል አዲስ ኪዳን በተጻፈበት ቋንቋ υἱοθεσία ሁዮቴሲያ መሆኑንም አይተናል። ልጅ መሆን፥ ልጅ መደረግ፥ እንደ ልጅ መወሰድ ማለት ነው። እኛ በክርስቶስ በኩል የእግዚአብሔር ልጆች ተደርገናል። ታዲያ ተደርገናል የሚለው ያልበቃቸው ሰዎች ከክርስቶስ ጋር እኩያ የሆኑ ልጆች እንደሆኑ ራሳቸውን ያሳብጣሉ። ልጅነት ሥልጣን ቢሆንም (ዮሐ. 1፥12) በሥልጣናችን የተቀዳጀነው ሥልጣን ሳይሆን የተሰጠን ሥልጣን ነው። ይህንን υἱοθεσία ሁዮቴሲያ የሚለውን ቃል ብዙዎቹ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች the adoption of sons ወይም the adoption of children ብለው ተርጕመውታል። ትክክለኛ ትርጉም ነው። አንዳንድ ሰዎች ማደጎ እና ጉዲፈቻ የሚለውን ቃል ይጠቀማሉ። ይህ ቃል በአገራችን አሉታዊ የሆነ ምስል ስለሚቀርጽ ለአንዳንዶች ግራ ያጋባል። ያጋባ እንጂ ነገሩ ግን ያ ነው።

በአገራችን ባህል ቃሉ አሉታዊነት የተጫነው ይሁን እንጂ፥ አዲስ ኪዳን በተጻፈበት ዘመንና ዐውድ ይህ ቃልና ልማድ ግን ድንቅ ነገር ነው። በአገራችን ማደጎ ተደርገው የሚወሰዱ ልጆች፥ ችግረኞች፥ አሳዳጊ ያጡ፥ ምስኪኖች፥ ድሀ አደጎች፥ ወላጅ አልባዎች ናቸው። እንደዚህ ብቻ ብንወስደውም እንኳ ትርጉሙ ያስኬዳል። እኛም እኮ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጆች ከመሆናችን በፊት ምስኪኖችና ከጸጋ የራቅንና ከክብሩ የጎደልን፥ የወደቅን፥ የሞትን ሙታን ነበርን! ጳውሎስ ይህንን በጻፈበት የግሪክ ወሮሜ ባህልና በአዲስ ኪዳን ዘመን ችግረኛ ሕጻናት ብቻ ሳይሆኑ ትልልቅ ሰዎችም ልጆች ተደርገው ይወሰዳሉ። ወሳጁ ሰው ደግሞ ልጆች የሌሉት ወይም ያሉትም ሊሆን ይችላል። ልጆች ከሌሉት ያንን ልጅ አድርጎ የወሰደውን ሰው ወራሹ ሊያደርገው ከመፈለጉ በጎነት የተነሣ ብቻ ነው ልጅ የሚያደርገው። ልጆች ካሉትም አብሮ ወራሽ እንዲሆን፥ የልጆቹ ወንድም እንዲሆን፥ ቸርነቱ እንዲበዛ ሲል ልጁ ያደርገዋል፤ እኩል መብትም ያቀዳጀዋል። ልጁም በስሙ ይጠራል። ይህ የበጎነት ምልክት ነው።

እግዚአብሔር እኛን ልጆቹ ያደረገን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ነው። በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን። በውድ ልጁም እንዲያው የሰጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ። ኤፌ. 1፥5-6።

የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነትስ?

የመለኮት ባሕርይ ተካፋይ ወደሚለው አሳብ እንምጣ። የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት ጥቅስ በ2ጴጥ. 1፥4 የሚገኘው ነው። ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን። 2ጴጥ. 1፥4

የአማርኛው ትርጉም ገና ሲጀምር በዓለም የሚገኝ ጥፋትን የሚያመጣ ክፉ ምኞትን በመግለጥና ከዚያ ማምለጥን በመናገር ይጀምራል። መለኮት መለኮት መጫወት የሚያምራቸውን ሰዎች ስናይ መጀመሪያ የምናስተውለው ነገር፥ ከዚህ ክፉ ምኞትና ዓለማዊ ጥፋት የራቁ ሳይሆኑ የተጣበቁ መሆናቸውን ነው። ከዓለምና የዓለም ከሆነ ነገር ጋር እየተጫወቱ የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነትን ማውራት ይመቻል? አይመችም። ዓለምን እንደ ሙጫ ተጣብቀውባት፥ ስጋዊነትን ተላብሰው፥ ገንዘብን እንደ ውኃ እየተጠሙና እየጠጡ የባሕርይ ልጆች ነን ሲሉ ያስደነግጣል።

የመለኮት ባሕርይ በሚለው ሐረግ ውስጥ፥ ‘መለኮት’ ግልጽ አሳብ ስለሆነ፥ ‘ባሕርይ’ የሚለውን ቃል እንመልከት። መለኮት አምላክነት ነው። አምላክ አንድ ብቻ ነውና እኛ በፍጥረታችን አምላክነት የለንም። ባሕርይ የሚለው ቃል በተጻፈበት በግሪክ ቋንቋ φύσις ፉሲስ ወይም ፊሲስ የሚል ነው። ቃሉ ምን ማለት እንደሆነ በሌሎች የተጠቀሰባቸው ቦታዎች ማየት ተገቢ ነው። ቃሉ በአዲስ ኪዳን ወደ 11 ጊዜያት ተጽፎአል። አራቱ ጥቅሶች ባሕርይ ሲሉ የቀሩት ፍጥረት ይሉታል። ፍጥረት የሚለው ቃልም አሳቡን ይገልጠዋል።

2ጴጥ. 1፥4 ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን።

ሮሜ 1፥26-27 ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ሴቶቻቸውም ለባሕርያቸው የሚገባውን ሥራ ለባሕርያቸው በማይገባው ለወጡ፤ ስለምንድር ነው የሚናገረው? ሴቶች ፍጥረታቸውን ወይም ሴትነታቸውን ትተው ከሴትነታቸው ሌላ፥ የሴትነት ባሕርይ ወይም ተፈጥሮ ያልሆነውን ሌላ ለመሆን መሞከራቸውን ነው። ባሕርይ የተባለው የተፈጠሩበት ነገር ወይም ፍጥረታዊ ማንነት ወይም ውስጣዊ ማንነት ነው።

ሮሜ 2፥14 ሕግ የሌላቸው አሕዛብ ከባሕርያቸው የሕግን ትእዛዝ ሲያደርጉ፥ እነዚያ ሕግ ባይኖራቸው እንኳ ለራሳቸው ሕግ ናቸውና፤ ይህም የሚያሳየው ሰዎች ሰዎች ብቻ ስለሆኑ መለኮታዊውን ተሻጋሪ ሕግ ወይም የሕሊና ሕግ ሊኖሩት ሊታዘዙት በውስጣቸው እንደሚያውቁት ይገልጣል። ይህ ባሕርይ የተሰኘው ነገር የውስጥን ማንነት ገላጭ ቃል ነው። ለምሳሌ፥ አትግደል የሚለውን አምላካዊ ትእዛዝ ያልሰማና ያልተማረ ሰው፥ በፍጥረቱ መግደል መጥፎ መሆኑን ያውቃል።

ገላ. 4፥8 ነገር ግን በዚያን ጊዜ እግዚአብሔርን ሳታውቁ በባሕርያቸው አማልክት ለማይሆኑ ባሪያዎች ሆናችሁ ተገዛችሁ፤ ገላ. 4፥8 በባሕርይ አምላክ አለመሆን ግልጽ ነው። ምንም አምላክ የለም፤ ከአንዱ በቀር። አምላክ ተደርጎ የሚመለክ የለም ማለት አይደለም። ግን ያ ጣዖት እንጂ አምላክ አይደለም። ወይም መለኮት አይደለም። እነዚህ ጣዖታት ፍጥረቶች፥ ፍጡራን፥ ወይም አጋንንት፥ ወይም የሰው እጅ ሥራ የሆኑ ቅርጻ ቅርጽ ናቸው እንጂ አምላክ ወይም መለኮት አይደሉም። በባሕርያቸው፥ በማንነታቸው ወይም በምንነታቸው አማልክት አይደሉም። ውስጣዊ፥ የራሳቸው የሆነ፥ ፍጥረታቸው የሆነ፥ አምላክነት የላቸውም።

ይህ φύσις የተባለው ቃል ከላይ ባየናቸው ጥቅሶች ውስጥ ባሕርይ ተብሎ ሲተረጎም ወይም ሲሰኝ በተቀሩት ቃሉ በተጠቀሰባቸው ጥቅሶች በሮሜ 2፥27፤ 11፥21 እና 24፤ 1ቆሮ. 11፥14፤ ገላ. 2፥15፤ ኤፌ. 2፥3፤ ያዕ. 3፥7፤ ይኸው ተመሳሳይ ቃል (φύσις) በአማርኛ ፍጥረት እየተባለ ተተርጕሞአል። ፍጥረት ውስጣዊ ማንነት ነው። ባሕርይን በሚገባ ይገልጠዋል። ደስታ ተክለ ወልድ ባሕርይን ሲተረጕሙ፥ ‘ያልተፈጠረ፥ የማይመረመር፥ የማይታወቅ፥ ኅቡእ፥ ረቂቅ፥ ቅድስት ሥላሴን አንድ የሚያደርግ፥ በሥርው፥ በጕንድ፥ በነቅዕ የተመሰለ፤ የፈጣሪ ባሕርይ፤ አምላክነት’ ይሉታል። ዐዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት፤ ገጽ 162። ከላይ ባየናቸው ጥቅሶች ውስጥ ባሕርይ የሚለው ውስጣዊ ማንነት ወይም ኹነትን ነው።

ቀደም ሲል በነገረ ክርስቶስ እና በነገረ ሰብዕ፥ የባሕርይ ልጅ እና የጸጋ ልጅ የሚለውን ስንመለከት የባሕርይ ልጅ ሲባል ከአድራጊው ጋር አንድ መሆንን አመልካች ነው። ይህ ለኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅነት የምንጠቀምበት የስነ መለኮት ቃል ወይም ሐረግ ነው። ባሕርይ የሚለው ቃል በአንዳንዶቹ φύσις የሚለው ቃል በተተረጎመባቸው ቦታዎች ተፈጥሮ ቢባልም፥ ለመለኮት ተፈጥሮ እንዳንለው ማሰብ አይመችም። ኢየሱስ ፍጡር አይደለምና የተፈጥሮ ልጅ አይባልም። ሥሪት እንዳይባልም እርሱ ሠሪ እንጂ ተሠሪ አይደለምና ይህም አያስኬድም። ኢየሱስ የባሕርይ ልጅ መሰኘቱ ወልድ እና አብ አንድ ባሕርይ ወይም በእንግሊዝኛ essence በግሪክ οὐσία ወይም ούσιος የተባለውን መሆናቸውንና የኒቅያው ጉባኤ አብ እና ወልድ አንድ ባሕርይ ὁμοούσιος ሆሞኡሲዮስ ወይም ὁμοούσιον ሆኖኡሲዮን መሆናቸውን ለመግለጥ እንደተጠቀመበት ተመልክተናል።

ቃሉ አንድ ዓይነትነትን ገላጭ ነው። ὁμός ሆሞ ወይም ሆሞስ አንድ ወይም አንድ ዓይነት ወይም ምንም ልዩነት የሌለው ተመሳሳይ፥ οὐσία ኡሲያ ባሕርይ። ይህንን ὁμοούσιος የሚለውን ሐረግ ወደ እንግሊዝኛ “consubstantial” ብለው ነው የተረጎሙት። ይህ የኒቅያ ጉባኤ አርዮስ የተወገዘበት ጉባኤ ነው። አርዮስ ኢየሱስ ከአብ ጋር አንድ ወይም እኩል ያልሆነ ከሰው የሚበልጥ ከአብ ግን ያነሰ ወይም ሙሉ መለኮት ያልሆነ ያደርገዋል። (አርዮሳውያን የሆኑ የዘመናችን የዋችታወር ተከታዮች ወይም የይሆዋ ምስክሮች ነን የሚሉ ኢየሱስ ከአብ ጋር አንድ ወይም እኩል ያልሆነ ከሰው የሚበልጥ ከአብ ግን ያነሰ ወይም ሙሉ መለኮት ያልሆነ የተፈጠረ ፈጣሪ ያደርጉታል።) ኋላ በ381ዱ የቁስጥንጥንያ ጉባኤም ይኸው መግለጫ ጸና።

 

The post የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች ነን? እንዴት? የእግዚአብሔር ልጆችስ ነን? እንዴት? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ዝነኝነት ወይንስ ታማኝነት? https://deqemezmur.com/2022/10/16/celebrity-or-loyality/ Sun, 16 Oct 2022 23:44:48 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2148 ጌታውም፦ መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው። ማቴ 25፥21 “አንተ ታማኝ ባሪያ” መባል ከምንም በላይ ሊያሳስበን የሚገባበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፤ በጌታ ፊት ዋጋ የሚሰጠው ታማኝ ባሪያ መሆን እንጂ ዝነኛ አገልጋል ሆኖ መገኘት አለመሆኑን ልናስተውል ይገባል፤ ታማኝ ሆኖ መገኝትን በተለያየ መልኩ የሚያሳንሱብን፣ ይሄንን ዋና የሆነውን ጥሪ እንዳናይ […]

The post ዝነኝነት ወይንስ ታማኝነት? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ጌታውም፦ መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው። ማቴ 25፥21

“አንተ ታማኝ ባሪያ” መባል ከምንም በላይ ሊያሳስበን የሚገባበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፤ በጌታ ፊት ዋጋ የሚሰጠው ታማኝ ባሪያ መሆን እንጂ ዝነኛ አገልጋል ሆኖ መገኘት አለመሆኑን ልናስተውል ይገባል፤ ታማኝ ሆኖ መገኝትን በተለያየ መልኩ የሚያሳንሱብን፣ ይሄንን ዋና የሆነውን ጥሪ እንዳናይ የሚጋርዱን ብዙ አይነት ነገሮች በዙሪያችን ከበውናል፤ በተለይ ዘመን አመጣሹ የሶሻል ሚዲያውም ሆነ እንደ ዝነኛ (Celebrity) ወይንም ፌመስ ዘማሪ፣ ፌመስ ሰባኪ የመደነቅ ነገር ለብዙዎች እንቅፋት እየሆነ ያለንበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፤

ወደ ዝነኝነት የመጡ ሰዎች ብዙ አይነት የሕይወት መንገድ ተጉዘው ወደ ዝነኝነት ማማ ላይ መውጣት የቻሉ ናቸው፤ ይሄ ዋጋ ያስከፈላቸው ጉዞ እና አሁን ያሉበት ክብር (STATUS) በቀላሉ ሊለቁት የማይችሉት ማንነት ሆኖ ያገኙታል፤ ይሄን አይነቱ ዝነኝነት ወደ ቤተ እምነት የገባ አደገኛ የሆነ አካሄድን እየተፈጠረ እንዳለ ማየት ይቻላል፤ እነዚህ በጌታ ቤት በዝነኝነት መንፈስ ራሳቸውን ከፍ ያደረጉ፣ ከመደዴው ምእመን በላይ እንደሆኑ የሚያስቡ፤ ጌታ የሰጣቸው ጸጋ፣ ታማኝ ሊሆኑ የተጠሩለትን ጥሪ ያጎደሉ፣ ቅባታቸው ከተራው አማኝ ተርታ እንዳይመደቡ ከዛም ባለፈ መልኩ የሚቀመጡበት ወንበር የተለየ፣ የሚለብሱት ልብስ በዋጋ የተወደደ አንዳንዶቹም የሚነዱት መኪና ለኔ ቢጤው ደሃ ሲታይ የሚያስደነግጥ እየሆነ ከመጣ ሰንበትበትብሏል፤

በታዋቂነት ማንነት ማገልገል እና ለቃሉ እውነት ታማኝ ሆነን በማገልገል መካከል ያለው መስመር በጣም ስስ ነው፤ በጳውሎስ እና ባርናባስ (ሐሥ 14፥8-19) ያለውን ታሪክ ስንመለከት የሚያስተምረን ነገር አለ፤ ጳውሎስ እና ባርናባስ በበልስጥራን በእነሱ የተደረገው ተአምር ምክንያት “ሕዝቡም ጳውሎስ ያደረገውን ባዩ ጊዜ፣ በሊቃኦንያ ቋንቋ፣ “አማልክት በሰው ተመስለው ወደ እኛ ወርደዋል!” ብለው ጮኹ፤” (ሐሥ 14:11) ይሄ የሚያሳየን ቀጣዩ ነገር እነ ጳውሎስን ለየት ያለ ስፍራ መስጠት ከዛ ባለፈ መልኩ ልዩ በሆነ መልኩ እነሱን ትንንሽ አማልክት ማድርገ ማምለክ ነበር የዚያ ከተማነዋሪዎች ፍላጎት። የጳውሎስ እና ባርናባስ ምላሽ ግን ““እናንት ሰዎች፤ ለምን ይህን ታደርጋላችሁ? እኛም እኮ እንደ እናንተው ሰዎች ነን” የሚል ነበር፤ ምክንያቱም ታማኝ ሊሆኑለት የሚገባ ጥሪ የነበራችው ሰዎች ስለነበሩ፤

ይሄን መስመር በምን ያክል እንዳለፍን አንዳንዴ በማይገባን መልኩ አልፈነው ልንገኝ እንችላለን፤ ቤተ ክርስቲያን በተለይ በሰዎች ዘንድ የተለየ ዝነኝነት ያተረፉ ሰዎች እንዲያገለግሉም ሆነ በመድረኮቻቸው እንዲገኙ ሲሽቀዳድሙ መመልከት ለዚህ አይነቱ ችግር የበለጠ መባባስ ምክንያት ከሆኑ ነገሮች መካከል አንዱ ነው፤ “ከልካችን ያለፈ ጉርሻ መዋጥ ትንታ ያተርፋል። እግዚአብሔር በሰጠን ልክ ለክብሩ በመኖር ፈንታ የየራሳችን ትንንሽ ጣዖታት ለመሆን ባንጋጠጥን ጊዜ በድንገት መፈንገልን እናተርፋለን።” (የዱባ ጥጋብ ገጽ 118 በሰሎሞን አበበ ገብረ መድኅን)

ዝነኛ ሰዎች በተለየ መልኩ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የበለጠ እንዲታወቅ የተለየ አስተዋጽዖ ያደርጋሉ ብዬ አላምንም፤ ነገር ግን በእነዚሁ ሰዎች አማካኝነት ጌታ አይሠራም ማለቴም እንዳልሆነ እንዲታወቅልኝ እፈልጋለሁ፤ በጣም ጌታን የሚፈሩ በታማኝነት እርሱንና እርሱን ብቻ የሚያገለግሉ፣ በሚያገለግሉት ጌታም ሆነ የአገልግሎታቸውን በረከት ተካፋይ በሆነ አማኝ መካከል ስፍራ ያላቸው ወገኖችም እንዳሉ ማሰብ ተገቢ እንደ ሆነ አምናለሁ፤ “በጌታ የተቀበልኸውን አገልግሎት እንድትፈጽሙው ተጠንቀቅ በሉልኝ።” (ቆላ 4፥17) ብሎ ጳውሎስ ለአክሪጳ እንዳስጠነቀቀው በዙሪያቸው የሚታየው ግርግር እና ጭብጨባ ሳይሆን ለተቀበለው አገልግሎት ጥንቃቄ እንዲያደርግ ያስጠነቅቀዋል፤

‘ከዚህም የተነሣ ዝናው በመላዋ ሶርያ ተሰማ፤ ‘ማቴዎስ 4:24

በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አገልግሎት እየሆነ ከነበረው ነገር የተነሳ ለየት ያለ እውቅናን አግኝቶ ነበር፣ ከመታወቅም አልፎ እንደውም ስላበላቸው ስላጠጣቸው፤ “’ኢየሱስም ሰዎቹ መጥተው በግድ ሊያነግሡት እንዳሰቡ ዐውቆ እንደ ገና ብቻውን ወደ ተራራ ገለል አለ።” (ዮሐንስ 6:15) በዚህ የዮሐንስ ወንጌል ታሪክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባደረገው ነገር ዝናን አትርፎ ነበር ነገር ግን ከዝነኝነት የተነሳ የሚመጣ ክብር ከሚያስገኝልን ምስጋና ይልቅ ይዞብን የሚመጣው ጣጣ ብዙ መሆኑን ሊያስተምረን ስለፈለገ ራሱን ገለል አደረገ እንጂ ለማሱ (ለብዙሃኑ) ግርግር ራሱን አልሰጠም፤

ራስን እንደ ማወቅ እና ራስን እንደ መሆን ትልቅ ነገር የለም፤ ይሄ በሕይወታችን መሆን ሲችል ያን ጊዜ ለታማኝነት የቀረበ ልቦናን እናገኛለን፤ ራሳችንን መሆን የሚያስችለን ብቸኛው ነገር ለእግዚአብሔር ቃል የተጠጋ ማንነት ሲኖረን ነው፤ የቃሉ መስታወት ማንነታችንን ለራሳችን በማጋለጥ ልካችንን እንድናይ ያደርገናል እግዚአብሔርን የትኛውንም ያክል ብናውቀው ልንላመደው አንችልም ለዚህ ነው ራስን ማወቅ ልክን ማወቅ ነው። ጌታ ጌታ  ነው እኛ እኛ ነን፤ ጴጥሮስ ከጌታ ኢየሱስ ትንሳኤ በኋላ ስለ ራሱ ያለው እይታ ለየት ያለ መሆን ችሎ ነበር፤ በፊት ፈጠን ፈጠን ይል የነበረው አሁን ግን “…..ጌታ ሆይ፤ አንተ ሁሉን ታውቃለህ፤ እንደምወድድህም ታውቃለህ” አለው።” ወደሚለው ራስን ወደማወቅ መጣ፤ (ዮሐ 21፥17)

የተቀበልነው አደራ ተጠያቂነት ያለበት ስለሆነ ታማኝነት ግድ ይላል፤ ልባም ባሪያ ሆነን ስንገኝ የተሰጠንን አደራ ለተደራሹ እንደሚገባ ተጠንቅቀን እናደርሳለን፤ ለዚህ አይነቱ ባሪያ ትልቁ ትኩረት ተደራሹ አይደለም አደራ የሰጠው ነው ትልቅ ስፍራ ያለው!! “’ጌታም እንዲህ ሲል መለሰ፤ “እንግዲህ፣ ምግባቸውን በተገቢው ጊዜ እንዲሰጣቸው፣ ጌታው በቤተ ሰዎቹ ላይ የሚሾመው ታማኝና ብልኅ መጋቢ ማነው? ‘ሉቃስ 12:42

የተቀበልነው አደራ ራሳችንን ልናሳይበት ሳይሆን ልንጠነቀቅለት፣ ራሳችንን እኛነታችንን ዝቅ ልናደርግለት፣ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ በምድረበዳ የምንጮህ ድምጽ የምንሆንለት እንጂ የምንታይ ዝነኞች እንዳልሆንን ሊገባን በዚህ መልኩ ራሳችንን ልናውቅ ይገባል፤

‘እርሱ ሊልቅ፣ እኔ ግን ላንስ ይገባል። ‘ዮሐንስ 3:30

 

The post ዝነኝነት ወይንስ ታማኝነት? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
በዝማሬ አምልኮ ዙሪያ https://deqemezmur.com/2022/10/04/on-worship-and-singing/ Tue, 04 Oct 2022 23:43:44 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2125 በወንድም ለዓለም ጥላሁን (ላሊ) የተጻፈ በጸሃፊው ፈቃድ በዚህ ድረ ገጽ ላይ ወጥቷል በአምልኮ ጊዜ: የምናመልከው (ምናልባት ባለማስተዋል) ራሳችን በምናባችን እንደመሰለን የሳልነውን “አምላክ” ሳይሆን ራሱን በቃሉና በመንፈሱ የገለጠውን ህያው እግዚአብሔርን መሆኑን እርግጠኞች እንሁን!! የዝማሬ አምልኮአችን ይዘትና ጥልቀት ጥራትና ፍሬያማነት እንዲለወጥ ከአምልኮ በፊት የምናደርገው ቅድመ ዝግጅት ወሳኝነት አለው- በቴክኒክ ብቻ ሳይሆን በመንፈስ!! የሚመለከው ማነው? የሚለውን ጥያቄ በአግባቡ […]

The post በዝማሬ አምልኮ ዙሪያ first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
በወንድም ለዓለም ጥላሁን (ላሊ) የተጻፈ በጸሃፊው ፈቃድ በዚህ ድረ ገጽ ላይ ወጥቷል

በአምልኮ ጊዜ:
የምናመልከው (ምናልባት ባለማስተዋል) ራሳችን በምናባችን እንደመሰለን የሳልነውን “አምላክ” ሳይሆን ራሱን በቃሉና በመንፈሱ የገለጠውን ህያው እግዚአብሔርን መሆኑን እርግጠኞች እንሁን!! የዝማሬ አምልኮአችን ይዘትና ጥልቀት ጥራትና ፍሬያማነት እንዲለወጥ ከአምልኮ በፊት የምናደርገው ቅድመ ዝግጅት ወሳኝነት አለው- በቴክኒክ ብቻ ሳይሆን በመንፈስ!!
የሚመለከው ማነው? የሚለውን ጥያቄ በአግባቡ ስንመልስ የአምልኮአችን አቅጣጫ በትክክለኛው የልብ ቅኝት መገራቱ አይቀሬ ይሆናል!! መረሳት የሌለበት ቁምነገር ግን ዝግጅቱ የሚደረገው ቅዳሜ ማታ ወይም ዕሁድ ጠዋት ሳይሆን ከሰኞ እስከ ሰኞ ሊሆን የግድ መሆኑ ነው!! አምልኮ የሚያነጣጥረው በተመላኪው ላይ ብቻ ነው! ሁለት ተሞጋሾች ሁለት ተወዳሾች ሁለት ተደናቂዎች የሉም! ተመላኪው አንድና አንድ እርሱም “ያለና የሚኖር እኔ ነኝ” ያለው እግዚአብሔር ብቻ ነው!!
አምልኮ በተመላኪው ስምና ዝና ላይ ተንጠላጥለን ለራሳችን አድናቆት የምናተርፍበት ሳይሆን በተመላኪው ፊት ሁለንተናችንን ዝቅ አድርገን በትህትና “እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ይገባኛል” የምንልበት መንፈሳዊ አሰራር ነው!!
1. አምልኮ በየዕለቱ ከተመላኪው ጋር የሚደረግ የቅርበት ግንኙነት የወለዳቸው የትናንሽ ደመናዎች ጥርቅም እንጂ ድንገት የፕሮግራም ቀን ሳይታሰብ የሚከሰት የበረከት ዝናብ አይደለም! በልባችን መሰዊያ ላይ እንደበራ የሚቀጥል የየዕለት የህይወት ዘይቤ እንጂ የፕሮግራም ለት ክስተት አይደለም!
2. በአምልኮ ሰዓት
መዝሙሩና ሙዚቃው ከመቃኘቱ በፊት ልብ መቃኘት አለበት! ሙዚቃው የመዝሙሩን ዜማ ሳይጀምር በፊት የአምላኪው ልብ በራሱ ዜማና melody አምልኮ መጀመር መልመድ ይኖርበታል! ምክኒያቱም እግዚአብሔር አስቀድሞ የልባችንን ዕጣን ሳያሸት የዝማሬያችንን ዕጣን አያሸትምና!!
3. ሳያዩ ማምለክ ስለማይቻል ለማምለክ መገለጥ ይጠይቃል! እግዚአብሔር በዚህ ሳምንት ስለራሱ ምን ገለጠልን? ምን በራልን ነፍሳችን ምን ተረዳች? ምን አወቀች?
የሚገርመው ነገር አንድ ጠብታ መገለጥ አንድ አገር አምልኮ ይወልዳል! ከብዙ መዝሙር ይልቅ በመገለጥና በጥልቅ መረዳት የተዘመረ አንድ ወይም ጥቂት መዝሙር ረጅም መንገድ ያስኬደናል! በአንፃሩ ደግሞ በዛሬ ዓመቱ መገለጥ ብቻ ብዙ ርቀት መሄድ አስቸጋሪ ሆኖ እናገኘዋለን!
4. አምልኮ ስጦታ ይዞ መቅረቢያ ሳይሆን ራስን ስጦታ አድርጎ ማቅረቢያ ነው!
ለዚህ ነው: “ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ህያው ቅዱስም መስዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ….እለምናችሁዋለሁ” ብሎ ሃዋርያው ጳውሎስ በአፅንዖት የሚያሳስበን (ሮሜ 12:1)
5. አምልኮ የሰውን ሁለንተና ይጠይቃል! ከላይ ያለው ጥቅስ “ሰውነታችሁን” ሲለን ስጋችሁን ማለቱ አይደለም! ሁለንተናችሁን አቅርቡ እያለን ነው – ስሜትን ፈቃድን ሃሳብን ነፍስን ስጋንና መንፈስን!!

The post በዝማሬ አምልኮ ዙሪያ first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
አምልኮ ‹‹ምንነቱ፣ እንዴትነቱ እና ለምንነቱ›› https://deqemezmur.com/2022/10/03/worship-the-meaning-and-the-how/ Mon, 03 Oct 2022 19:49:33 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2076 ይህ ጽሁፍ በወንድም ረታ ጳውሎስ የተጻፈ ነው፤ በጸሃፊው ፈቃድ በዚህ ድረ ገጽ ላይ ወጥቷል፤ ክፍል 4 ባለፉት ክፍሎች እንዲሁ በግርድፉ የዘመናችንን ቤተ ክርሰቲያን የዝማሬ አምልኮ ሥርዓት ግድፈቶች እና መሰናክሎች በማንሳት ለመነጋገር ሞክረናል፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ባሉ ክፍሎች የአምልኮ ትርጉም፣ መርህ እና አላማ በአጭር በአጭሩ ለመዳሰስ እሞክራለሁ፡፡ “አምልኮ” የሚለው ቃል ውስጥ ሶስት ዋና ዋና ጉዳዮችን እናስተውላለን፤ አምላክ፣ […]

The post አምልኮ ‹‹ምንነቱ፣ እንዴትነቱ እና ለምንነቱ›› first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ይህ ጽሁፍ በወንድም ረታ ጳውሎስ የተጻፈ ነው፤ በጸሃፊው ፈቃድ በዚህ ድረ ገጽ ላይ ወጥቷል፤

ክፍል 4
ባለፉት ክፍሎች እንዲሁ በግርድፉ የዘመናችንን ቤተ ክርሰቲያን የዝማሬ አምልኮ ሥርዓት ግድፈቶች እና መሰናክሎች በማንሳት ለመነጋገር ሞክረናል፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ባሉ ክፍሎች የአምልኮ ትርጉም፣ መርህ እና አላማ በአጭር በአጭሩ ለመዳሰስ እሞክራለሁ፡፡ “አምልኮ” የሚለው ቃል ውስጥ ሶስት ዋና ዋና ጉዳዮችን እናስተውላለን፤ አምላክ፣ መስዋዕት እና አምላኪው፡፡ ሶስቱ ጉዳዮች በአግባቡ ተሳልጠው ልከኛ ቦታቸውን ካልያዙ አምልኮ የሚባለው ነገር ክሳቴ አይኖረውም፡፡ አምላክ (Object of Worship) ሲሆን አምልኮን ተቀባይ ወይም የድርጊቱ መንስኤ፣ ዋና ምክንያት ነው፡፡
                                                                                “አምላክ ስላለ ነው አምልኮ የኖረው!
በማንኛውም ሀይማኖት እና እምነት (ቃልቻ፣ ቦረንትቻ፣ ሌላም ቻ..) የአምልኮ ነገሮች ተመሳሳይ ናቸው፡፡ እኛ የምንነጋገረው ስለ ዓለማቱ ፈጣሪ ታላቁ አምላክ ዘለዘለማዊው እግዚአብሔር ነው፡፡ መስዋዕት ለአምላክ የሚሰጥ ስጦታ ወይም ምላሽ ሆኖ የሚቀርብ ጥልቅ ፍቅር፣ እምነት፣ ከፍተኛ አድናቆት (ውዳሴ)፣ ፍርሃት (እየወደድነው እንፈራዋለን)፣ መንቀጥቀጥ (የአክብሮት ጥግ)፣ መንዘፍዘፍ፣ ድንጋጤ (ሰቦማይ ይላል ግሪኩ)፣ ራስን እስከ መሳት ያለ ከፍተኛ አድናቆት (ራዕይ 1፡17)፣ መገዛት ሲሆን፥ ይህ ደግሞ በሶስት ምልዓተ ደርዝ ይገለጣል፡፡

  1. የሀሳብ አምልኮ (Worship in Thinking)
  2. የአንደበት አምልኮ (Worship in singing or speech)
  3. የሥራ አምልኮ (Worship in action)
  4. የሀሳብ አምልኮ ምንድነው?

ስለ አምላካችን እግዚአብሔር በልባችን ያለው ፍቅር፣ አክብሮት፣ ፍርሃት፣ አድናቆት እና እምነት ነው፡፡ ሀሳብ በጣም የሚገርም ፍጥረት፣ የማንነታችን ክፍል ሲሆን ለሰዎች ሊታይ ፈጽሞ የማይችል የአዕምሮ ቀመር ነው፡፡ በዓለም ያሉ ጠቢባን ሳይነቲስቶች የሰውን የተለያዩ የአካል ክፍሎች በዝርዝር የሚያሳዩ፣ የመጠቁ መሳሪያዎችን ሰርተዋል፡፡ የጭንቅላት ዕጢ፣ የደም መፍሰስ፣ የነርቭ ችግሮችን፣ የተሰበረ አጥንት… ወዘተ ለማየት ችለዋል፡፡ CT SCAN, MRI, X-RAY, ULTRASOUND… ብዙ ነገሮችን ማሳየት የቻሉ የሰው ልጅ ረቂቅ የጥበብ ውጤቶች ናቸው፡፡ ነገር ግን የቱንም ያህል ቢራቀቁ የሰውን ሀሳብ ለማየትና ለመገንዘብ አልቻሉም፡፡ ሃሳባችን በማንም አይታይም ለዚህም ነው እንደ ፈለግን የምናስበው፡፡ ከሰዎች ጋር አብረን ስንኖር እርስ በርስ ሀሳባችንን መተያየት የምንችል ቢሆን ኖሮ ምን ይሆን ነበር? ስለ ባልንጀራችን የምናስበውን ሁሉ የሚያውቅ መሳሪያ ቢኖር በእውነት በምድር እንኖር ነበር ወይ?

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሀሳብ ምን እንደሚል ጥቂት ብቻ እንመልከት፡፡
ኢያሱ 18 የዚህ ህግ መጽሐፍ ከአፍህ አይለይበቀንም በሌሊትም አስብ፤ ያን ጊዜ መንገድህ ይቀናልሃል፡፡
መዝ. 12-3…በእግዚአብሔር ህግ ደስ ይለዋል፣ ህጉንም በቀን እና በሌሊት ያስባል እርሱ በውሃ ፈሳሾች ዳር እንደተተከለች ፍሬዋን እንደምትሰጥ፣ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፣ የሚሰራውም ሁሉ ከናወንለታል።
ፊል. 48 በቀረውስ ወንድሞች ሆይአስቡ
ቆላ 31 በላይ ያለውን አስቡ እያለ ምን ያህል ሀሳባችን ከፍ ያለ ንጹህ እና ቅን ሊሆን እንደሚገባው ቃሉ በአጽንኦት ይናገራል፡፡

አምልኮ ስለ እግዚአብሔር በልባችን ከምናስበው በጎ ነገር ካልጀመረ ይፈርሳል!! ‹‹በሀሳብህ ያላከበርከው ጌታ መድረክህ ላይ አይከብርልህም››!! በልብህ ያላነገስከው ጌታ ድንገት በደመቀ ተቀጣጣይ ዝማሬ አይነግስልህም! የጊታርህ ክር፣ ድምጽህም ቢቃኝ ሀሳብህ ካልተቃኘ ፈርሷል! ዛሬ ሀሳባችንን የሞላው ነገር ምን ይሆን? ሀሳባችን እና መዝሙራችን ይተዋወቃሉ?፣ ይቀራረባሉ? ወይስ በየፊናቸው እየተመሙ ነው? በቀን እና በሌሊት የምናስበው ጉዳይ በመድረክ እና በጉባኤ ከምንዘምራቸው ዝማሬዎች ጋር በእውነት ዝምድና አለው ወይ? ካልሆነ ድርሰተ ተውኔት እየተወንን ብቻ እንጂ እያመለክን አይደለም፣ አፍርሰናል፡፡ በዋልድባ የዘፈነ ዲያቆን አፍርሷል እንደሚባለው እንዲሁ ልንዘፍን አይገባም፡፡ የሀሳብ ጥራት በሌለበት የአንደበታችን ስል ንግግር ሆነ ዜማ እግዚአብሔርን ሊያስደስተው አይችልም፡፡

ምስጋናችን ጥልቅ እንጂ ግልብ ሊሆን አይገባም፡፡ “ግልብ” ምስጋና ቆሌ የሌለው እንዲሁ የሙዚቃ ምት እየተከተሉ የሚሉትንም ሳያውቁ መደሳሰት መፈንጠዝ አይነት ሲሆን:- “ጥልቅ” ምስጋና ግን ከጥልቅ ልባችን የሚፈልቅ፣ በቂ ምክንያት ያለው፣ የጌታ ምህረት ብዛቱ በባለውለተኝነት ስሜት እያናወጠን፣ እንባ እንባ እያለን ወይም የሚፈነቅል ደስታ ሲያስጮኸን ነው፡፡ ደስታም እኮ ጥልቅ እና ግልብ ልዩነቱ ያስታውቃል፡፡ ማንም በማያየው የሀሳባችን ስፍራ እኔ ልንገስ እያለ ነው ጌታ፡!!

አንደበታችን ለሰው ነው፣ ተግባራችንም ለሰው የሚታይ ነው፣ ፍርድ ቤት ዳኛ በንግግርህ አልያም በስራህ እንጂ በሃሳብህ ሊፈርድብህ አይችልም፡፡ እንደዚህ እያሰብክ ነው ስለዚህ ጥፋተኛ ነህ ቢል ዳኛ እንዴት እንግዳ ነገር ይሆን? ለእግዚአብሔር ብቻ በተለየችው የሀሳባችን መሰዊያ አምልኮን ብንጀምር አትጠራጠሩ ሁሉ ይሰምራል፡፡ ልባችን ልክ አይደለም!! ከዚህም የተነሳ በእውነተኛ አምልኮ ልንባረክበት ከሚገባን በረከት በብዙ ጎድለናል፡፡ ፊል 4፡8 ቃሉ “በቀረውስ ወንድሞች ሆይ እውነተኛ የሆነውን…ንጹህ የሆነውን፣ ፍቅር ያለበትን፣ መልካም ወሬ ያለበትን…ወዘተ አስቡ” ሲለን እኛ ሁሉን በተቃራኒው እያሰብን ቢሆንስ? ማር 12፡28 በፍጹም ልብህ፣ ሃሳብህ፣ ነፍስህ እና ሐይልህ ጌታ አምላክህን ውደድ ሲል እኛ በፍጹም ሪትም፣ ፒች፣ ቅኝት፣ ጩኸት፣ ላይት፣ ጪስ፣ መድረክ፣ ልብስ ብቻ ልንወደው ሞክረን ይሆን? ልብም፣ ነፍስም፣ ሀሳብም፣ ሀይልም የውስጥ ናቸው በመሰረታዊ ደረጃ፡፡ ስለዚህ ጊታራችን ኪቦርዳችን ላይን አሬያችን ምርጥ እንደሆነ ሁሉ ሀሳባችን ምርጥ ይሁን!! ስለ ጌታ፣ ስለ ባልንጀራ፣ ስለ ሀገር፣ ስለ ህዝብ ያለን ሀሳብ በጎ ይሁን፡፡ አጥብቀህ ልብህን ጠብቅ!! መዝ 19፡14 የአፌ ቃል እና የልቤ ሀሳብ በፊትህ ያማረ ይሁን፡፡ ሀሳብ ሲያምር አንደበት ያምራል፣ ተግባርም ያምራል፡፡

 

 

The post አምልኮ ‹‹ምንነቱ፣ እንዴትነቱ እና ለምንነቱ›› first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ግን ምንድን ነው፣ ኀልዎቱ የመለኮቱ? https://deqemezmur.com/2022/10/01/what-dose-the-presence-of-god-meaning/ Sat, 01 Oct 2022 22:06:04 +0000 https://deqemezmur.com/?p=2029 ከሰሎሞን ጥላሁን ፌስ ቡክ ገጽ የተገኘ ጽሁፍ እግዚአብሔር ሳይከፋፈል ሳያንስና ሳይበዛ በፍጥረተ ዓለሙ ሁሉ በሙላቱ ይገኛል፣ ይህ ጠባዩ omnipresence/ “ክሳቴ ኩሉ” ይባላል። ድብልቅልቅ ባለው የመርካቶ ግፊያ መሃል ያለ አንድ ገበያተኛ በጠፈር ምርምር ማርስ ላይ የወጣ ጓደኛው ስልክ ደውሎ እግዚአብሔር በዚህ አለ ቢለው መርካቶ መሐል ካለው ማንነቱ የተሻለና ንጹህ ማንነት አለው ማለት አይደለም። እነዚህ የእኛ ርቀቶች […]

The post ግን ምንድን ነው፣ ኀልዎቱ የመለኮቱ? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>
ከሰሎሞን ጥላሁን ፌስ ቡክ ገጽ የተገኘ ጽሁፍ

እግዚአብሔር ሳይከፋፈል ሳያንስና ሳይበዛ በፍጥረተ ዓለሙ ሁሉ በሙላቱ ይገኛል፣ ይህ ጠባዩ omnipresence/ “ክሳቴ ኩሉ” ይባላል። ድብልቅልቅ ባለው የመርካቶ ግፊያ መሃል ያለ አንድ ገበያተኛ በጠፈር ምርምር ማርስ ላይ የወጣ ጓደኛው ስልክ ደውሎ እግዚአብሔር በዚህ አለ ቢለው መርካቶ መሐል ካለው ማንነቱ የተሻለና ንጹህ ማንነት አለው ማለት አይደለም። እነዚህ የእኛ ርቀቶች ለእግዚአብሔር በኢንች አይራራቁበትም፣ ሥፍራዎች ሳይፈጠሩ በፊት የነበረው በስፍራዎች ሁሉ ሳይቀናነስ አለ- መገኛዎቹ ግን እርሱነቱ አይደሉም … በብሉይ ለምሳሌ ታቦቱን አስመልክቶ ሲስቱ፣ “ታቦቱን ይዘን ጦርነት ብንወጣ ድል እናደርጋለን” አሉ እነርሱም አለቁ ታቦቱም ተማረከ። የመገኛው ምሳሌና እርሱ ራሱን ሲያምታቱ ሳጥን ውስጥ እንደማይገባላቸው አሳያቸው! …ለምሳሌ በአዲስ ኪዳን አማኞች  ሲስቱ “የመለኮት ማደሪያ መለኮት ነን አሉ”፣ (አፌ ቁርጥ ይበል) ግማሾቹም ሞቱ ያሉትም አሉ በሙተት ላይ። ስለዚህ ከእኛ ጋር ነው እንጂ እኛን አይደለም!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!

ይህ ሳይርቅ መቅረቡ “አባታችን ሆይ” እንድንል ሲያደርገን፣ ረቂቅና ምጡቅነቱ (ትራንሴንደንስ) “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ” እንድንል ያደርገናል። ክርስትናን ልዩ የሚያደርገው ይህ ነው።  ስለዚህ እየቀረብነው እንፈራዋለን እየፈራነው እንወደዋለን!

የህልውናው ስሜት የመገኘቱ መገለጥ ነው እንጂ የሆነ ቦታ የሄደው ሲመጣ አይደለም፣ “እግዜር ” ለአፍታ በመሄዱ የተነሳ የሌለበት ቦታ ሊኖር አይችልም፣ እነዚህ ሁሉ መለዋወጦች ያሉት እኛ ዘንድ ነው። እኛ ከዚያ ስንመጣ ያለነው እዚህ ነው፣ ከዚህ ስንሄድ ያለነው እዚያ ነው! ለእግዜር ግን ህልውናው በመጠን አይቀናነስም። የእግዚአብሔር መገኘት እኛ ሲሰማን ከሆነ ቦታ መጣሁ ብሏቸው አደለም እኛ ዘንድ ያለው – ኢያኢሮስ ይሔ ስለገባው ነው ጌታን “ባትሔድም እዚያ ነህ ብቻ ቃል ተናገር” ያለው። እዚህ የእድሜ ልክ ደም ፍሳሽ ሲያቆም በዚያው ሰከንድ እዚያ ማዶ ከመቅሰፍት ሞት ይመልሳል! ሉቃስ 8:41-56 ስለዚህ እቅርብ ላለው ጉዳያችን ደሜን አቁምልኝ ስንለው ሩቅ ያለውን ጉዳያችንን ከሞት አስነሳልኝ የማለት የእምነት ድፍረት ይፈቀድልናል!

የእግዚአብሔር የህልውናው ተሰምቴዎቻችን መለዋወጥ እኛ ዘንድ ካሉ ልምምዶች ጋር የተያያዙ ናቸው። ምንም እንኳ የህልውናው ስሜት ለሁላችንም “እነሆ” የተባለ ቢሆንም፣ ሁላችንም አንድ ዓይነት ስላልሆንን በተመሳሳይ አንለማመደውም! እድሜ፣ ያለንበት መንፈሳዊ ደረጃ፣ የመንፈሳዊ የህይወት ተሞክሮ፣ የምንሰጠው ጊዜ “ሊትል ኢንቲሜሴ ሊትል ካፓሲቲ” አለ [ቶኒ ኤቫንስ] ልምምዶቻችን ይለያያሉ፣ ሁላችንም ግን መንፈሳችን ክፍት ነው … ለህልውናው መነካኪያ ቅባሪ የሰው ልጅ ሁሉ አለው። ስለዚህ በምንም ዓይነት መንፈሳዊ ሁኔታ ውስጥ ብንሆንም የኅልውናውን ስሜት አለመፈለግ ከተፈጠርንበት አላማ በታች ለመኖር መወሰን ነው! እግዚኦ በሉ አንድ ጊዜ ፟_ ስንት ቀን ነው ያለዚህ ስሜት መኖር የምትችሉት? እነሆ ምርጫው የእናንተው ነው፣ አማኝ ሆኖ እንደ አላማኝ መኖር ….

እግዚአብሔር የህልውናውን ስሜት ከሌሎች የተሻለ ነጥሎ ለእገሌ አብዝቶ የሰጠው የለም “ኤልያስ እንደኛው ሰው ነበረ ..” ማለት ይኽው ነው…. እንዲያውም ብዙ ጊዜ ስፍራ የሚያናውጠው በማህበር ሲያገኘን ነው፤ የሐዋ 2፡… እነርሱም ስፍራውም ተናወጠ ዘጸ 40 … ተራራው ጤሰ – ስለዚህ ስንሰበሰብ ኅልውናው ይሰማናል ወይ? ስንሰባሰብ የማን ኅልውና ይሰማናል? ወንድሞች በኅብረት …
እግዚአብሔር እዚህ/እዛ ነው እንጂ እዚህ ብቻ እና እዛ ብቻ አይደለም። በክርስትና አስተምህሮ ሁለት የእግዚአብሔር ሀልዎት መገለጫ ቃሎች አሉ መለኮታዊ ምጡቅነቱና መለኮራዊ ቅርበቱ (138 ፡7)…  እግዚአብሔር ሳያንስና ሳይበዛ ያለ መስፈሪያ አለ።

ሀ. ወደ ላይና ወደ ታች 7- 8 የምታወቀው በምድር ላይ ስላለሁ ነው ብዩ ወደ ሰማይ ብመጥቅ ቀድመኸኝ አገኝሃለሁ ወደ ታችኛው ጥልቁ ብሔድ የዚህም ሥፍራ ዳኛ አንተ ሆነህ አገኝሃለሁ (አሞጽ 9:2)
ለ. ምስራቅና ምእራብ 9-10 ላይና ታች ባይደብቁኝ ንጋት በሚነጋበት በምስራቁ በኩል በማለዳ ተነስቼ ጸሐይ ሳትጠልቅ እንደ ንስር ሁለት ሜትር ክንፍ ባወጣና ወደ ምእራብ ብሸሽ ያ ይረዳኝ ይሆን? ለዚህ እንኳ ቀድመኸኝ መንገዱን ያበጀኸው አንተ ነህ –  በሁሉ ሥፍራ በአንድ ጊዜ ለሚገኘው ጌታ ምስራቅና ምእራብ የለውም ሁሉም ነገር ለእርሱ እዚህ ጋ ነው!!!!!  ስለዚህ ካንተ ሽሽት ከእግዜር ወጥቶ ወደ እግዜር መግባት ነው ካለ በኋላ – ከጅረት ወደ ወንዝ፣ ከወንዝ ወደ ሐይቅ፣ ከሐይቅ ወደ ባህር ከውሃ ወደ ውሃ

እግዚአብሔር በስፍራዎች ሁሉ ይገኛል ማለት ስፍራዎች ሁሉ እግዜር ናቸው ማለት አይደለም። እግዚአብሔር የመገኛዎቹም ድምር ውጤት አይደለም – ይኽ ፓንቴይዝም ነው እግዚአብሔር እዚህ እዛ ነው እንጂ እዚህ ውስጥ አይደለም። ለእግዜር የቀረበ ነጥብ ላይ ያለ ማንም የለም፣ ለዚህ ነው አማላጅ የሚባለው ነገር የማይሰራው” እንደታዋቂ ሰዎች አንተ ትቀርበዋለህ አናግርልኝ አይባልም። የስላሴ አካል እግዜር ሰው የሆነው ክርስቶስ ብቻ ነው ይህን ሚና የሚጫወት-  እግዚአብሔር ቁስ አይደለም በቅርበትና በርቀት ከ ጀምሮ እስከ አይባልም. “አለ” የሚለው ቃል የማይሰራበት የፍጥረቱ ክልል የለም። መዝ 139 ፡7-13

ስለዚህ፦ መንፈሳዊ ቦታ ነው ብለን ያልንበት ቦታ ስንገኝ የምናሳየው ጥንቃቄና ሌላው የህይወታችን ቦታ የምናሳየው አንድ ዐይነት ሊሆን ይገባል:: ይኼ እኮ ቤተ ክርስቲያን ነው እንዲህና እንዲህ አይባልም አይደረግም እንላለን እዚህ ያለው እዚያ የለም ወይ?

The post ግን ምንድን ነው፣ ኀልዎቱ የመለኮቱ? first appeared on ደቀ መዝሙር.

]]>